Saturday, April 4, 2015

ፋሲካ !

                                ለብርሃነ ትንሳኤው እንኩዋን አደረሳችሁ!

'' ወይቤሉን ፡ አትደንግፃ፡፡ ኢየሱስሃኑ፡ ናዝራዊ፡ተኀሥሡ፡ ዘተሰቅለ፡፡ ተንሥአ፡ ወኢሀሉ፡ ዝየስ፡ ወናሁ፡ መካኑ፡ ኀበ፡ ተቀብረ፡፡ ''
 /እርሱ ግን እንዲህ አላቸው፡ አትደንግጡ፡ የምትፈልጉት የተሰቀለውን የናዝሬቱን ኢየሱስን ነው፡ እርሱ ተነስቶአል፡ እዚህ የለም፡ እርሱን ያኖሩበት ስፍራ ይኸውላችሁ፡፡/ ማርቆስ 16፤6

 ጌታችን ፣ መድኀኒታችን ና አምላካችን  ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ሁላችን በደል እና ሐጢያት መከራን ተቀብሎ በመስቀል ላይ ከሞተ በሁዋላ ፡ በሶስተኛው ቀን ከሞት ተነስቶአል፡፡ ይህ ብርሃነ ትንሳኤው ነው በመላው ዓለም የፋሲካ በዐል ተብሎ  የሚታወቀው ፡፡

ፋሲካ የስሙ ትርጉዋሜ ማለፍ  ማለት ሲሆን፤ ይህም እስራኤላውያን ከ 430 በግብጽ በባርነት አገዛዝ ከነበሩበት አሰጨናቂ ዓመታት ነጻ የወጡበት ቀን ነው፡፡ በዚያም ቀን ምሽት በሁሉ ቤት ታርዶ የነበረው ጠቦት ፣ በበራቸው ጉበንና በመቃናቸው የለቀለቁት ደም ምሳሌነቱ ክርስቶስና የክርስቶስ ደም ነው፡፡ጌታችን እኛን ከሐጢያትና ከኩነኔ ሊያድነን ዋጋ ከፍሎአል፡፡ አሁን በአዲስ ኪዳን ዘመን ከ ዓለም ልንወጣ የምንችለው ደግሞ የአዲስ ኪዳኑን / የፋሲካውን በግ / በማመንና በመቀበል ሲሆን ፣ በቀራኒዮ በፈሰሰው ደሙም ከሚመጣው ቁጣ ማምለጥ እንችላለን፡፡ ደሙን በጉበኑ ባላደረገ ቤት ሁሉ ሞት እንደነበረ፡ በክርስቶስ ደም ያልነጻ እና የደሙ ማህተም በግንባሩ የሌለ ማንኛውም ሰው ከዘላለም ሞትና ፍርድ ማምለጥ አይችልም፡፡

እርሶም ዛሬ ከግብጽ  / ከዓለም / ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ በክርስቶስ አምልጠው አውነተኛውን የክርስትና ህይወት ሊኖሩ የሚወስኑበት ጊዜ እንዲሆን እመኝልዎታለሁ፡፡ በዛሬዋ ቀን በመስቀል ላይ ስለ እርሶ ሞቶ የተነሳውን ጌታ ና መድሓኒት በልብዎ ውስጥ ስፍራ ይስጡት፡፡ እስቲ የቀረዎትን  ዘመን ለሞተውና ለተነሳው ጌታ ሊሰጡት ዛሬ ይወስኑ! እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይረዳዎታል፡፡

                                                                              መልካም የትንሳኤ በዓል ይሁንልዎ!!!

      


  ማስታወሻ፡-  ይህንን መልዕክት ፋሲካውን እያከበሩ ላሉ ወዳጅ  ዘመዶቻችን ሁሉ ሼር እናድርግ!

                                                                                                          benjabef@gmail.com

orthodox mels kaalaat 3

Monday, March 30, 2015

በሰሞነ ህማማት!

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን በድምቀት ከሚታሰቡና ከሚከበሩ በዐላት መካከል የሰሞነ ህማማት አንዱ ነው፡፡

   ጌታችን መድሀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ዓለም ሁሉ ሐጢያት በመስቀል ላይ ከመሞቱ ጥቂት ቀናት በፊት በቃላት ሊነገር የማይችል ስቃይና መከራ ውስጥ እንደነበረ የአይን እማኞች ጽፈዋል፤ መስክረዋልም፡፡ ያ የህማሙ ሳምንት ነው ፡ ሰሞነ ህማማት ተብሎ የተሰየመው፡፡ ጌታችን በእነዚያ ቀናት ተጨንቆ ነበር፣ የደም ላብ አልቦት ነበር፣ ስድብና ውርደትን ሁሉ ተቀብሎአል፤ ይህ ሁሉ ስለ እኛ ነበር፡፡ ነቢዩ ኢሳያስ ስለ መከራው እንዲህ ነበር የተናገረው፡-

  " ከመ ፡በግዕ፡ አሞጽእዎ፡ ይጠባሕ፡ ወከመ፡ በግዕ፡ ዘኢይነብብ፡ በቅድመ፡ ዘይቀር፡ ከማሁ፡ ኢከሰተ፡ አፋሁ፡ በሕማሙ፡፡ወተንሥአ፡ እምኩነኔ፡ ወእምነ፡ሞቅሕ፡ ወመኑ፡ ይንገር፡ ልደቶ፡እስመ፡ ትትእተት፡ እምድር፡ሕይወቱ፡፡ / ተጨነቀ ፣ ተሰቃየም አፉንም አልከፈተም፣ለመታረድ እንደሚነዳ ጠቦት በሸላቶቹም ፊት ዝም እንደሚል በግ እንዲሁ አፉን አልከፈተም፡፡ በማስጨነቅ ና በፍርድ ተወሰደ፤ ስለ ሕዝቤ ሀጢያት ተመትቶ ከሕያዋን  ምድር እንደተወገደ ከትውልዱ ማን አስተዋለ? '' ኢሳይስ 53፡ 7 ና ሥራ. 8፤32-33

የህማሙን ሳምንት እንዴት ማሰብ ይጠበቅብናል?

  ምዕመናን ሁሉ ሐጢያታቸውን  በሚናዘዙበት ጊዜ  እውነተኛ ንስሐ  እና መድሐኒዓለም ክርስቶስ ስለ በደላችንና መተላለፋችን የከፈለውን ዋጋ በፍጹም ልብ  ማመንና መቀበል ይገባል፡፡
 ሐጢያት በመጀመሪያ እግዚአብሔር በላከው በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ አለማመን ሲሆን በመቀጠል አለመታዘዝን ጨምሮ እንደ ዘፈን፣ ስካር፣ ዝሙት፣ ጣኦትን ማምለክ፣ ጥልና ክርክር የመሳሰሉት የስጋ ስራዎች እንደሆኑ በገላቲያ.5፤16-19 ላይ ተዘርዝሮአል፡፡ ሁሉንም ሐጢያታችንን ለእርሱ ዘርዝረን ስንነግረው በደላችንን  ሁሉ ይቅር ሊለን እንደሚችል በቃሉ ተናግሩዋል፡፡ /1ዮሐ.1፤9/፡፡
 ነገር ግን ከዚህ በተቃራኒ ሐጢያት እንደሆኑ የሚታወቁ ስንት ጉዳዮች እያሉ ፡ ሐጢያት ተብለው በቃሉ ያልተጠቀሱትን  ለምሳሌ በህማማቱ የሰው እጅ እንደ መጨበጥና፣ ጥራጥሬዎችን መፍጨት ወይም ማስፈጨት ....ወዘተ እንደ ሐጢያት ሆኖ ቀርቦ ብዙ ሰዎች ባለማወቅ ያንን ውድ የሆነ የንስሐ ጊዜን  በትክክል ሳይጠቀሙበት  ሲቀሩ ይታያል፡፡ እርሶ ግን  ከእግዚአብሔር ጋር እውነተኛ  ህብረት ቢያደርጉ እና በግልጽ ሀጢያትዎትን ቢናዘዙ ከበደልዎ ሁሉ ይነጻሉ፡፡
  ከኑዛዜ በሁዋላ ያለው ህይወታችንም የተለወጠ እና ክርስቶስን የሚያከብር እንዲሆን ህይወታችንን ለመንፈስ ቅዱስ መስጠት ይጠበቅብናል፡፡ ዘውትርም በእግዚአብሔር ፊት መጸለይ እና ቅዱስ ቃሉን / መጽሐፍ ቅዱስን/  ማንበብ አስፈላጊ ነው፡፡

                     የሚከተለውን የንስሐ ጸሎት ከልብዎ ሆነው ይጸልዩ!

ጌታ ሆይ እኔ ኃጢያተኛ ነኝ፤ከልጅነት ጀምሮ እስከዚህ ቀን ድረስ ባለማወቅና በድፍረት የሰራሁትን 

ኃጢያት ሁሉ ይቅር  በለኝ፡፡ጌታ ኢየሱስ ሆይ ስለ እኔ ሐጢያት መከራን እንደተቀበልክ ፣ደምህን 

እንዳፈሰስክ ና እንደሞትክልኝ እምናለሁ፡፡ ስለ ሐጢያቴ በፈሰሰው ደምህ  ከበደሌ ሁሉ አንጻኝ 

፤ልጅህ አድርገኝ፡፡ ከዛሬዋ ዕለት ጀምሬ አንተን  የህይወቴ ጌታና አዳኝ አድርጌ  

እቀበልሀለሁ፡፡በልቤም ላ ይ ንገስ ! ስሜንም በህይወት መዝገብ ላይ ፃፍልኝ በኢየሱስ ክርስቶስ  ስም 

አሜን፡፡"

 ማስታወሻ፡-  ለቤተሰብዎ እና ለጉዋደኞችዎ  ይህንን እውነት ያጋሩአቸው !
                                                                                                                       
                                                                                                                   benjabef@gmail.com

Saturday, March 28, 2015

New Ethiopian Orthodox Sibket By Memehere Asegid Sahelu -Eyesus Ende Cheger

          ወይቤ መጽሐፍ ኩሉ ዘየአምን ቦቱ የሐዩ ሮሜ.10፤11
         / መጽሐፍ በእርሱ የሚያምን ሁሉ አያፍርም ይላል፡፡ /

     የጌታችን  የመድሀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ክቡር ወንጌል ለምዕመናኑ እያቀረቡ ላሉት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ልጆች ሁሉ እንጸልይላቸው፡፡ይህ የአቢይ ጾም እውነተኛ ንስሐ ገብተን ከአምላካችን ጋር የምንታረቅበት፣ የህማማቱን ሳምንት ብቻ ሳይሆን ስለ እኛ የታመመውንና የተገረፈውን ጌታ፣ የተሰቀለበትን ቀን ብቻ ሳይሆን ስለ እኛ የተሰቀለልንን ጌታ፣ የተነሳበትን የፋሲካ ቀን ብቻ ሳይሆን ስለ እኛ ሐጢያት ሞቶ የተነሳውን ጌታ፣ የምንቀበልበት ና ህይወታችን የሚለወጥበት መልካም የሆሳዕናና የፋሲካ ጊዜ ይሁንልን !አሜን፡፡

ማሰታወሻ፡- ይህንን መልዕክት ወደ ሌሎች ወገኖች ማስተላለፍዎትን አይዘንጉ፡፡

Friday, March 20, 2015

በ መሪጌታ ጽጌ ና መሪጌታ ሙሴ...






ለቤተሰብዎና ለጉዋደኞችዎ ያጋሩአቸው፤ እውነቱንም ያውቁ ዘንድ ወንጌልን ለህዝባችን ተባብረን እናገልግል፡፡ የወንጌል እውነትን ለመግለጥ ደፋ ቀና ለሚሉት ሁሉ እንጸልይ!
ይህ የተሐድሶ ዘመን ነው!!!

Saturday, March 14, 2015

ቀን ሳለ !

                                        
       . የእድሜህ  ዘመን ስንት ነው ?
     .  የሚሰራበት ቀንና ስለ ማይሰራበት ሌሊት አውቀዋልን?

                 የመግቢያ ጥቅሶች


''....ቀን ሳለ የላከኝን ስራ ልፈጽም ይገባኛል፡፡ ማንም የማይሰራባት ሌሊት ትመጣለችና፡፡'' ዮሐ.9፤4

''.....አንተ እንድሰራው የሰጠኸኝን ስራ ፈጽሜ በምድር አከበርኩህ ፡፡'' ዮሐ.17፤4

 እነዚህ ሁለት  ጥቅሶች የሚያስረዱት የመጀመሪያው የተሰጠንን ተልዕኮ እና ዓላማ በተሰጠን ቀን ቶሎ ልንፈጽመው እንደሚገባ እና በሌላ በኩል ደግሞ ቀኑ አልፎ ማንም ሊሰራባት የማይችልባት ሌሊት እንደምትመጣ ነው፡፡ ከተፈጥሮ እንደምንረዳው ቀን የሚባልና ሌሊት የሚባሉ ጊዜዎች አሉ፡፡መንፈሳዊውም ልክ እንደዚሁ ነው፤ ከተፈጠርንበት ዓላማ ጋር የምንሰራበት ጊዜም አብሮ ይሰጣል፡፡ እርሱን በዋዛ፣ በፈዛዛ ካሳለፍነው ደግሞ ቢመኙም እንኩዋ ከብዙ ነገር አንጻር ምንም ማድረግ የማይቻልበት ጊዜ ይመጣል፡፡
   ቀኖቻችን የተመቻቹ አጋጣሚዎቻችን  ናቸው፡፡ጤናችን አፍላ ጉልበታችን፣ የተትረፈረፈ ሰዓታችን ሊሆን ይችላል፡፡ብዙ ነገሮችን በቀላል መንገድ መስራት የሚያስችሉን የዘመነኛው ቴክኖሎጂዎችም በተወሰነ መልኩ መልካም አጋጣሚዎቻችን ሊሆኑልን ይችላሉ፡፡ ምናልባት አንዳንድ ህጎች፣ፖሊሲዎች...ወዘተ ቀን እንደሆነልን ሊጠቁመሙን ይችላሉ፡፡ ምናልባት ዛሬ ክፍት የሆኑ ነገሮች ነገ ላይዘጉ ፤ ዛሬ እንደልብ ልናገኛቸው የምንችላቸው ነገሮች ነገ  ላይወደዱ የሚችሉበት ምንም መተማመኛ ነገር የለም፡፡ የተትረፈረፈ  ጊዜያችን ነገ ላይ በጭንቅም ላይገኝ ይችላል፡፡መጠቀም ዛሬን ነው፡፡ የምንችለውን ሁሉ አድርጎ ማለፍ !

  ሁለተኛው ጥቅስ ደግሞ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምድር ሳለ የተሰጠውን ተልዕኮ በተሰጠው ጊዜ ጨርሶ በሰማይ ወደ ነበረው ክብር እንደሚመለስ ያለውን ነገር ነው የሚያስረዳው፡፡ ተልዕኮን በአንድ በተሰጠ ጊዜ ጨርሶ ፈጸምኩ ማለት እንዴት ደስ የሚያሰኝ ነገር ነው ?! ጳውሎስም ይህንኑ ነው ያለው .....ሩጫውን ጨርሼአለሁ ...........!

   በሰው ህይወት ሁሉ የምንሰራበት ቀን እና የማንሰራባት ሌሊት አለች፡፡አሁን ቀን የሆነላችሁ ፡ ማለትም ከብዙ ነገር አንጻር ነገሮችን ለማድረግ ዕድሉ የተመቻቸላችሁ፣ በመንገዳችሁ ላይ የይለፍ አረንጉዋዴ መብራት የበራላችሁን......የሚወክል ሲሆን፤ለሌሎች ደግሞ ሌሊት ውስጥ ያላችሁ ትኖራላችሁ ፡፡ ማለትም ምንም ነገር ለማድረግ ነገሮች ያልተመቻቸላችሁ፣ ማድረግ ብትፈልጉም ማድረግ ያልቻላችሁ፣ የጊዜ እጥረት ያለባችሁ፣ በመንገዳችሁ ላይ ቀይ መብራት ስለበራ ማለፍ የማትችሉትን ጭምር ማለት ነው፡፡ እንግዲህ ቀን ለሆነላችሁ በአግባቡ ጊዜውን እንድትጠቀሙበት ፣ ሌሊት የሆነባችሁ ደግሞ ተመልሶ  በቸርነቱ  ቀን  እስኪያመጣላችሁ በጸሎት በመትጋትና በእምነት ጠንክራችሁ እንድትጠብቁ እመክራለሁ፡፡

 ጊዜ ማለት ውድ ነገር ነው፡፡ የሚቆምበት እግር ያልተፈጠረለት ወፍ እንደማለት ነው ፡፡ ልናቆመውና እንዲጠብቀን ልናደርገው አንችልም፡፡ ለምሳሌ የትናንትናው ቀን   ተመልሶ ሊመጣ ይችላልን ? አይችልም፡፡ ልክ  ከአፋችን እንደወጣ ካርቦን ዳይኦክሳይድ  /የተቃጠለ አየር/ ነው፡፡ ያስወጣነውን አየር መልሰን ልናስገባ አንችልም፡፡ ተቃጥለው ያለፉ ጊዜዎችም ልክ እንደዚህ  ናቸው ፤ በነበራቸው ጊዜ አንዳች ሳይሰሩበት ከርመው በባነኑ ሰዐት ማጣፊያው ያጠራቸውና የቆጫቸው አያሌ ናቸው፡፡ የሌሊቱ ባህሪ ብዙ ጊዜ ጸጸትንና ቁጭትን ብቻ ነው የሚፈጥረው፡፡

   በዘፍጥረት 47 ላይ ፈረኦን የያዕቆብን ዕድሜ  ጠይቆት ነበረ፡፡ ‹‹..የእድሜህ ዘመን ስንት ነው? ለሚለው ጥያቄው የመለሰው ከቁጥር ጋር ክፉም ጥቂትም የሚሉ ቃላቶች ነበሩ፡፡እነዚህ ቃላት የሚያሳዩት በተለያየ ሁኔታ ስለ ተቃጠሉት ጊዜዎቹ ቁጭቱን ሲገልጽ ነው፡፡ ቢያንስ ሁለት ሰባት ዓመታቶች ሚስትን ለማግባት የተፈጁ እና ንጹህ ስድስት ዓመታት ደግሞ  የግልን ንብረት ለማከማቸት ያለፈ ጊዜ ነው፡፡ በርከት ያሉ የመከራ ዓመታትንም ከስደት ጋር አሳልፉአል፡፡

                         እድሜህ ስንት ነው ?
'' የዘመኖቻችን ዕድሜ ሰባ ዓመት ቢበረታም ሰማንያ ዓመት ነው፤ ቢበዛ ግን ድካምና መከራ ነው፡፡ ከእኛ ቶሎ ያልፋልና ፡እኛም እንገሰጻለንና ፡፡''መዝ.90፤10

በእግዚአብሔር ቃል ውስጥ በርካታ ክፍሎች ላይ ስለ እድሜያችን የተጠቀሱት ጥቅሶች የሚያስገነዝቡን ዕድሜያችን እምብዛም የሚያደላድል ና የሚያስፋፋ ነገር እንዳልሆነ ነው፡፡ በጣም ብዙ ዘመን እንደቀረው ሰው እንዳንኖር ትምህርት ይሰጠናል፡፡ ነገር ግን የሆነ ዓላማ ግን ፈጽመን ልናልፍበት እንችላለን፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ  ውስጥ ስለ ዕድሜያችን ምን እንደተባለ ቀጥለን ጥቂቶቹን እንመልከት፡-
  •  ዘመኖቻችን እንደ ሸረሪት ድር ይሆናሉ፡፡ መዝ.90፤9
  •  በከንቱ ይታወካል እንጂ በእውነት ሰው እንደ ጥላ ይመላለሳል፡፡ መዝ.39፤6
  •  ህይወታችሁ ምንድን ነው ? ጥቂት ጊዜ ታይቶ ሁዋላ እንደሚጠፋ እንፉዋሎት ናችሁና፡፡ ያዕ.4፤1
  •  .....እንደ ተን.....መዝ.38....
  • እንደ ሸማኔ መጠቅለያ፡፡ ኢሳ.38፡12
  •  
    ከላይ የተመለከትናቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች የሚያስረዱን ዘመኖቻችንን /'ዕድሜዎቻችንን'/ በቁም ነገር ላይ ካላዋልነው ና ለአንድ ለታለመ ዓላማ ካልተጠቀምንበት ዝም ብሎ ሊያልፍ የሚችልም ነገር እንደሆነ ጭምር ነው፡፡ እግዚአብሔር እድሜን የሰጠን በአቅማችን ሰርተን ማለፍ ካለብን ዓላማ ጋር ነው፡፡ በተለይ ሰዎችን ከዘላለም ሞት ከማዳን ዓላማ ጋር የተያያዘው ደግሞ የላቀው ነው፡፡አለዚያ ዘመናችን ውስን በሆኑና እዚህ ግቡ በማይባሉ አልባሌ ነገሮች ሊያልቁ ይችላሉ፡፡ ስንት ነገር መስራት የሚችል አዕምሮ በዋል ፈሰስ የቀረበት፣ የተፈጠሩበትን ዓላማ ሳያሳኩ ጊዜ ያለፈባቸው፣ ኸረ እንደውም የቀበርናቸው ስንት ናቸው፡፡ ከሚያሳሳው ጉልበታቸው ጋር፣ ችሎታና ብቃታቸው ጋር ያለፉትን ቤቱ ይቁጠራቸው፡፡ በዚህ ሁሉ ግን አሁንም ያልረፈደብን በርካቶች አለን፡፡ ቃሉ እንደሚል '' ደስ አያሰኙም የምትላቸው ዓመታት ሳይደርሱ፡ ብርሐን ወደ ጨለማ ሳይቀየር...ስጋም ወደ አፈሩ ሳይመለስ ነፍስም ወደ ሰጠው ወደ እግዚአብሔር ሳይመለስ ፈጣሪህን አስብ፡፡'' መክ. 12፤1-8፡፡

ሰዎችን ከማዳን ጎን ለጎን  ግን ህጻናትን የማሳደግ፣  ድሆችን የመመገብ፣ አረጋውያንን የመንከባከብ፣ የአካባቢና የተፈጥሮ ጥበቃን የመሰለ፣ ሌላም ሌላም ህብረተሰብን የሚጠቅም በጎ ራዕይ ሰርቶ ማለፍ ጥሩ ነገር ነው፡፡ በርካቶች ይህንን አድርገዋል፤ እያደረጉም ያሉ አሉ፡፡

በአንድ አገር ውስጥ የሰዎች ዕድሜ ላይ የሚያጠና አንድ ምሁር ሰዎች  የምድር ዘመን ቆይታቸው ሰባ ዓመት ቢሆን በዋናነት ዕድሜያቸውን በምን ጉዳይ ፈጅተውት እንደሚያልፉ በጥናት ካሰፈረው ነገር  ቀጥለን እናያለን፡-
  • ለእንቅልፍ 23  ዓመት / 32% /
  •  ለስራ 16  ዓመት  / 22% /
  •  የቴሌቪዥን ፕሮግራሞችን በመከታተል 8 ዓመት / 11%  /
  •  በመመገብ 6 ዓመት / 8.6% /
  •  በመጉዋጉዋዝ 6 ዓመት / 8.6%  /
  •  በመዝናናት 4.5 ዓመት / 6.5% /
  •  በተለያየ ህመም 4 ዓመት / 5.7%  /
  •  በመልበስ  2 ዓመት / 2.8% /
  • እንደ ጸሎት ያሉ የዓምልኮ ስርዐትን በመፈጸም 0.5 ዓመት / 0.9% /
      በእርግጥ አንዳንዶቹ እንደየ አካባቢው ሁኔታና እንደየ ህብረተሰቡ ዓይነት ሊለያዩ የሚችሉ ነገሮች ቢሆኑም፤አብዛኞቹ  ግን በብዙዎቻችን ህይወት ያጋጠሙና እያጋጠሙ ያሉ ነገሮች ናቸው፡፡ ከዚህም ውጪ ጊዜዎቻችንን በደንብ አድርገው እየጎመዱ ያሉ ነገሮች አይጠቀሱ እንጂ እንዳሉ እሙን ነው፡፡ እስኪ ጥቂት ጊዜ ወስደው የእርሶን ጊዜ በአብዛኛው እየፈጀ ያለ ጉዳይ ምን እንደሆነ ያስቡና ፡ በዓመት ያስሉት ፤ ከዚያ ወደ ሰባ ዓመት ይቀይሩት፡፡ በእርግጠኝነት  አንድ ነገር ይማሩበታል፡፡ በቀን የሚጸልዩትን ሰዐት ወደ ወር ፣ ደግሞ ወደ ዓመት ቢቀይሩም በጌታ ፊት ምን ያህል ጊዜ በዘመንዎ እንዳጠፉ ማወቅ አይቸግርዎትም፡፡  የተፈጠርንበትን ዓላማ በተሰጠን ዕድሜ በትክክል ፈጽመን እንድናልፍ እግዚአብሔር ይርዳን ! ጊዜያችን በከንቱ ያለቀብንና ዕድሜያችን የገፋም ካለን ፡ ምንም የማየይሳነው ጌታ ተምችና ኩብኩባ የበላብንን ዓመት እንዲ መልስልን ብንማጸነው ፣ ወይም እንደሶምሶን አንድጊዜ እንዲያስበንና የመጨረሻ ስራ ሰርተን እንድናልፍ ብንጠይቀው መልካም ነው፡፡ በእግር ኩዋስ ዓለም ያለ ምንም ግብ 90 ውን ደቂቃ ከጨረሱ በሁዋላ፡ በባከነ ሰዐት ግብ አስቆጥረው ፣ ድል  አድርገው እንደሚወጡት ቡድኖች  ሊሆን ይችላል፡፡ እግዚአብሔር አምላክ በነገር ሁሉ ያግዘን ፡፡ አሜን፡፡

ማስታወሻ፡-  ውድ ጊዜያቸውን ለከበረ ዓላማ እንዲያውሉት ለሚሳሱላቸው ሰዎች ይህንን  መልዕክት ያጋሩአቸው፡፡
                                                                                                     
                                                                                                benjabef@gmail.com

New Ethiopian Orthodox Preaching by Memhir Asegid- ነፍሴ የወደደችዉን አገኘሁት