Sunday, October 4, 2015

ሚስጥረ ቁርባን

''ሲበሉም ኢየሱስ እንጀራን አንስቶ ባርኮ ቆርሶም ሰጣቸውና እንካችሁ ይህ ስጋዬ ነው አለ፡፡ ጽዋውንም አንስቶ አመስግኖ ሰጣቸው ሁሉም ከእርሱ ጠጡ፡፡ እርሱም ይህ ስለ ብዙዎች የሚፈስ የአዲስ ኪዳን ደሜ ነው፡፡ '' ማርቆስ 14:22-23

  በተለያየ ጊዜ የሚነሱ ጥያቄዎች
  • ስጋዬን የበላ ደሜን የጠጣ የዘላለም ህይወት ያገኛል፡፡ ስለሚል ቁርባን ያጸድቃልን ?
  • ቅዱስ ቁርባን በቅዳሴ ጊዜ ወደ እውነተኛ የክርስቶስ ደምና ስጋነት ይቀየራልን ?
  •  ስጋውና ደሙን መውሰድ ያለበት ማን ነው? የሚሉትና የመሳሰሉትን መሰረታዊ ጥያቄዎች እንዳስሳለን፡፡
   በኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ከተደነገጉት 7 ዓይነት ሚስጥራት መካከል አንደኛው ሚስጥረ ቁርባን በመባል ይታወቃል፡፡ ቅዱስ ቁርባን  ወይም የጌታ እራት ብለን የምንጠራው ስርዓት የተደነገገው በጌታ እንደሆነ ይታወቃል ፡፡ይሁን እንጂ እስራኤላውያን ከግብጽ ባርነት ነጻ ከወጡበት ዕለት ጀምሮ እንዲፈጽሙት በእግዚአብሔር የታዘዙ በመሆኑ እስከዛሬ ድረስ ይጠብቁታል፡፡ ነገር ግን ብሉይ ኪዳን የአዲስ ኪዳን ጥላ በመሆኑ ና ክርስቶስ የገዛ ደሙን አፍስሶ ከሐጢያታችን አጥቦ ከዓለም ስላወጣን አርነታችን እውነተኛ ፋሲካ ክርስቶስ ሆኖልናል፡፡ ስለዚህም በጌታ እራት ጊዜ በድምቀት የምናስታውሰው ትልቁ ነገር የጌታ ሞትና ትንሳኤ ነው፡፡ የፋሲካ እውነተኛ ትርጉሙም ስለ ሐጢያታችን የሞተው የእግዚአብሔር በግ ክርስቶስ ነው፡፡

  ከጊዜ ወዲህ ግን ስለ ጌታ እራት ወይም ስለ ቅዱስ ቁርባን የሚሰጡ ትርጉሞች እንደየ ቤተ እምነቱ ሁኔታ መለያየትን አምጥቶአል፡፡ ለመሆኑ የጌታን እራት በመውሰድ ይጸደቃልን ? ይህ ዋነኛ ጥያቄ በቅድሚያ መመለስ አለበት፡፡ ብዙዎች የጌታን እራት በመውሰዳቸው ምክንያት እንደሚጸድቁ ሊያስቡ ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ጽድቅን ለማግኘት መጽሐፍ ቅዱስ የሚያስተምረን እውነት ከዚህ የተለየ ነው፡፡ ፅድቅ እንዴት ይገኛል? ብለን በሌላ ትምህርት ላይ አንስተን እንደነበረ ልብ በሉ ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚያስረዳን ጽድቅ ክርስቶስን በማመን የሚገኝ ነው፡፡ ዮሐ.3፤16፣ ሮሜ.6፤20፣ ሮሜ 10፤9፡፡ ታዲያ '' በስጋዎ ደሙ ይጸደቃል'' የሚለው ትምህርት ከየት የመጣ ነው ? ካልን በዮሐንስ ወንጌል 6 ላይ ከተጠቀሰው ቃል መነሻ ተደርጎ እንደመጣ የሚታመን ሲሆን ቃሉም '' ስጋዬን የበላ ደሜን የጠጣ የዘላለም ህይወት አለው አለ፡፡'' ቁ.54 ይላል፡፡

   ክፍሉን በጥንቃቄ ብናጠና ከመጀመሪያው ጀምሮ ስለ ምን እንደሚያወራ መመልከት ይቻላል፡፡ ከቁ.1-14  ብዙ ሰዎች ፡ማለትም ሴቶችና ህጻናትን ሳይጨምር ወንዶች ብቻ 5 ሺህ  ሆነው ወደ ጌታ የመጡበት ፣ከዚያም 2 ዓሳ ና 5 የገብስ እንጀራን ባርኮ ሁሉም እንደሚፈልገው ወስዶ ጠግቦ 12 ቅርጫት ቁርስራሽ የተነሳበት ታሪክ እናነባለን፡፡ ከዚያ ቁ. 15 ላይ ህዝቡ ኢየሱስን በድንገት ነጥቀው  ለማንገስ ሐሳብ እንዳላቸው አውቆ ከእነርሱ ፈቀቅ እንዳለ ያስረዳል፡፡ ከቁ.16 እስከ 25 ድረስ ህዝቡ በተለያየ ቦታ ፈልገው ፈልገው ፡በሁዋላ ላይ ግን እንዳገኙትና አንድ ጥያቄ እንደጠየቁት ተጽፉዋል፡፡ '' መምህር ሆይ ወደዚህ መቼ መጣህ? አሉት፡፡ ኢየሱስም መልሶ እውነት አውነት እላችሁዋለሁ የምትፈልጉኝ እንጀራ ስለበላችሁና ስለ ጠገባችሁ ነው እንጂ ምልክቶችን ስላያችሁ አይደለም፡፡ለሚጠፋ መብል አትስሩ፤ ነገር ግን ለዘላለም ህይወት ለሚኖር መብል የሰው ልጅ ለሚሰጣችሁ ስሩ፡፡እርሱን እግዚአብሔር አብ አትሞታልና፡፤ እንግዲህ የእግዚአብሔርን ስራ እንድንሰራ ምን እናድርግ አሉት'' ኢየሱስም መልሶ ይህ የእግዚአብሔር ስራ እርሱ በላከው እንድታምኑ ነው አላቸው፡፡'' ቁ.27-29፡፡ ቁልፍ ነገሩ እዚህ ጋር ነው ያለው ፡፡ ምዕራፉ የሚተነትነው ስለሚበላ የስጋ ምግብ ሳይሆን በክርስቶስ ስለማመን ነው ፡፡ ከዚያ በሁዋላ ያሉትን ጠቅላላ ቁጥሮች ብንመለከት ክርስቶስ ኢየሱስ ራሱን በማመን ስለሚገኝ የዘላለም ህይወት እርሱም የህይወት እንጀራ በመሆኑ '' የህይወት እንጀራ እኔ ነኝ፡፡ ወደ እኔ የሚመጣ ከቶ አይራብም፤በእኔ የሚያምንም ከቶ አይጠማም፡፡'' ቁ.35

  በእርግጥ ስጋዬን ብሉ ደሜን ጠጡ በሚለው ትምህርቱ ደቀ መዛሙርቶቹ እንኩዋ ሰምተው እንደተሰናከሉ እናነባለን ፡፡ የጌታ መልስ ግን '' ህይወትን የሚሰጥ መንፈስ ነው እንጂ ስጋ ምንም አይጠቅምም ፤እኔ የነገርኩአችሁ ቃል መንፈስ ነው ህይወትም ነው፡፡'' ቁ.63፡፡ ስለዚህ ቃሉ በአጠቃላይ ስጋዎ ደሙን ወይም የጌታ እራት የሚባለውን ስርዓት ለማስረዳትና ትዕዛዝ ለመስጠት የተጻፈ አይደለም፡፡ እርሱን የተነናገረበት ሌሎች ክፍሎች አሉ፡፡ ክፍሎቹ በሙሉ የሚያስረዱት የጌታ እራትን በመውሰድ ስለሚገኝ ጽድቅ ሳይሆን ፡ ድነት ያገኘንበትን ሞቱን እንድናስብ ነው፡፡ ለነገሩ ከስቅለቱና ከሞቱ በፊት የጌታን እራት በመውሰድ እንድንጸድቅ አስቦ ቢሆን፡ ለምን ያን ሁሉ ዋጋ ይከፍላል?፡፡ የመስቀል ላይ ጣሩ፣ የደሙ መፍሰስና ሞቱ በእርሱ አምነን እንድንድን የግድ አስፈላጊ ና ለሐጢያታችን ክፍያ መሆን ስለነበረበት የተደረገ ነው፡፡ ስለ ጽድቅም እርስ በርሱ የሚጋጭ ነገር አልተጻፈም፡፡ የጽድቅ መንገድ እርሱ እንዳለው '' እኔ መንገድ፣ እውነትና ህይወት ነኝ፡ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም '' ዮሐ.14፤6 ፡፡ ብሎአል፡፡ የጽድቅ ብቸኛ መንገድ ክርስቶስ ነው፡፡

    የጌታ እራት ትክክለኛ ትርጉም ምንድን ነው?
  • የጌታን ሞትና ትንሳኤ መናገሪያ/ማወጂያ/
  •  የቅዱሳን ህብረት ማድረጊያ፡፡ ይህም በአንድነት በምንወስደው ማዕድ በክርስቶስ የተሰጠንን ክርስቲያናዊ ህብረት የበለጠ እናጠናክራለን፤እርስ በርስም እንተናነጻለን፡፡/1ቆሮ.10፡16-18
  •  የምንባርከው የበረከት ጽዋ ከክርስቶስ ደም ጋር ህብረት ያለው ነው፡፡ ስለሆነም ከቅዱሳን የእርስ በርስ ግንኙነት በተጨማሪ ከጌታችንም ጋር ህብረት እናደርጋለን፡፡ ቁ.21
የጌታን እራት ማን ሊወስድ ይገባል?
  • የጌታን እራት በክርስቶስ ያመኑ አማኞች ሁሉ ሊወስዱት ይችላሉ፡፡
  •  አንዳንድ ቦታ እንደየ አካባቢውና ህብረተሰቡ ተጨባጭ ሁኔታ ቤተክርስቲያን በአወሳሰድ ጉዳይ የራሱዋን ድንጋጌ ልታወጣ ትችላለች፡፡ ይህም ስርዓቱ መንፈሳዊ ትርጉሙን እንዳያጣ እና እንደ ቆሮንቶስ ቤተክርስቲያን ሁኔታ እንዳይፈጠር በማሰብ ነው፡፡ 1ቆሮ.11፤17-31
  •  በሐጢያት ለመቀጠል ያልወሰነ አማኝ ሁሉ ራሱን መርምሮ መውሰድ ይችላል፡፡
   በእርግጥ ብዙ ጊዜ  ከጌታ ይልቅ፡ ለጌታ እራት የመጠንቀቅ ልማድ ብዙ ምዕመናን ላይ ይስተዋላል፡፡ ይህ ማለት ልባችን ውስጥ ያለውን ክርስቶስን በመፍራት ንስሐ ልንገባ፣ የበደሉንን ሰዎች ይቅር ልንል ወይም ይቅርታ ልንሰጥ ይገባል እንጂ የጌታ እራት በመጣ ቁጥር ብቻ የምንቀደስና የምንሩዋሩዋጥ ከሆነ፡ ድንገት የሚሆነው ምጻቱ ጊዜ ምን ሊውጠን ነው? ከዚህ በተጨማሪ ድል እና ድነትን ያገኘንበትን የሞቱን መታሰቢያ፡ የሙታን ተስካር እንደሚዘከር ያለ ስርዓት ማካሔድም ተገቢ አይደለም፡፡ ምክንያቱም በሞቱ ነው ሰይጣን ድል የተደረገው ፣ ሞትና መውጊያው የተሸነፉት፡፡ ሞቱ  ፣ የደረሰበት መከራና እንግልት ሁሉ ቢያሳዝነንም ግን ደግሞ በትንሳኤ የተነሳ ጌታ ነው፡፡ በዕለቱ  የንስሐ መንፈስ ያስፈልጋል ፡ደግሞ ደስ ሊለንና ልንዘምርም ይገባል፡፡

ትርጉሙ ሳይገባን መውሰድ የሚያስከትለው ቅጣት:-
  •  ሳይገባው የጌታን እራት የሚወስድ የጌታ ስጋና ደም ባለ ዕዳ ይሆናል፡፡1ቆሮ.11:27
  • ፍርን ያመጣል፡፡ ቁ.29
  •  ቆሮንቶሶች በጊዜው እንደ ደረሰባቸው አይነት ህመምና ሞት ጭምር ሊከሰት ይችላል፡፡ 1ቆሮ.11፡30
ስለሆነም ወደ ከበረው ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እራት ከመቅረብዎ በፊት ሁለት ወሳኝ ነገሮን መወሰንዎን አይዘንጉ ፡-

1-እውነተኛ ንስሐ መግባትዎትን

2-ስለ ዓለም ሁሉ ተሰቅሎ የሞተውን ደግሞ በሶስተኛው ቀን የተነሳውን መድኀኒዓለም ክርስቶስን ማመንዎትን እርግጠኛ ይሁኑ፡፡ ይህ ሲሆን አይደለም ለጌታ እራት ፡ለመንግሰተ ሰማይም እንኩዋ አይሰጉም፡፡ እግዚአብሔር አምላክ በነገር ሁሉ ያግዘን ፡፡ አሜን!