Saturday, April 25, 2015

በክፉ ቀን

በክፉው ቀን....

'' ስለዚህ በክፉው ቀን ለመቃወም ሁሉንም ፈጽማችሁ ለመቆም እንድትችሉ የእግዚአብሔርን እቃ ጦር ሁሉ አንሱ፡፡'' ኤፌ.6፤10-19

   የክፉው ቀን የቱ ነው?  የክፉው ቀን መቼስ ነው?

    ልክ እንደ አሁኑ ጊዜ ማለት ነው ፡፡ ብዙ ፈተና የበዘዛበት፣ የጸለዩት የማይሰማበት የሚመስልበት ቀን፤ ለጠላት የተፈቀደለት ቀን ይመስላል፡፡ ምናልባትም የዓለም ፍጻሜ ቀን የመጨረሻዎቹ ደቂቀ ላይ እንገኛለን፡፡ ስለዚህም ምጡ በዛ፣ እጅግ ዘግናኝና አሰቀቃቂ ነገሮች እየተከናወኑ ነው፡፡ ማስቆም አልተቻለም፣ ደግሞስ የቱን ከየትኛው ማስጣል ይቻላል? ብዙዎች በየቤታቸው እንቆቅልሽ ውስጥ ናቸው ያሉት፣ የፈተናው ና የመከራው ዓይነት ብዙ ነው፡፡ በፍጹም ያልጠበቅነው ነገር ገጥሞናል፡፡ በዚህ ከፉ ቀን የብዙዎች አቅም የሚፈተሸበት ፣ ጉልበታቸው የሚላላበት.፣ እምነታቸውን የሚፈትን ነገር የሚገጥምበት .....ጊዜ ነው፡፡

  በሕይወት ያልታሰበ  ነገር ሲገጥም ያስደነግጣል፤ ቢሆንም የመጨረሻው ዘመን ባህሪ በመሆኑ ልንታገስ ደግሞ ይገባል፡፡ ሐዋርያው ጳውሎስ ለልጁ ለጢሞቴዎስ እንደጻፈለት '' ነገር ግን በመጨረሻ ቀን የሚያስጨንቅ ዘመን እንዲመጣ ይህን እወቅ ሰዎች ራሳቸውን የሚወዱ ይሆናሉና ፣ገንዘብን የሚወዱ ፣ትምክህተኞች ፣ትዕቢተኞች፣ ተሳዳቢዎች፣ ለወላጆቻቸው የማይታዘዙ፣ የማያመሰግኑ፣ ቅድስና የሌላቸው ፣ፍቅር የሌላቸው፣ ዕርቅን የማይሰሙ ፣ሐሜተኞች ፣ራሳቸውን የማይገዙ ፣ጨካኞች፣ መልካም የሆነውን የማይወዱ ፣ከዳተኞች ፤ችኩሎች፣ በትዕቢት የተነፉ፣ ከእግዚአብሔር ይልቅ ተድላን የሚወዱ፣ ይሆናሉ፤ የአምልኮት መልክ አላቸው ኀይሉን ግን ክደዋል ከእነዚህ ደግሞ ራቅ፡፡" 2ጢሞ.3፤1-5

ማናችሁም ሰዎች የሆነባችሁ ነገር ከዚ ውጪ አይሆንም ብዬ እገምታለሁ፤ የሚያስጨንቀውን ዘመን ሁላችንም እየቀመስነው ነው፡፡ በዚህ ወቅት የሚያስፈልገው መጽናት ብቻ ነው፡፡

  አንዳንዱ ነገር ለምን እንደሆነብን እና እንደሚሆን ላይገባን ይችላል፡፡ አንገታቸውን በሰይፍ የሚቀሉ ሰዎች ብዛት፣ በህክምና ስህተት ያሳደጉዋቸውን ወላጆች የሚያጡ ሰዎች ብዛት፣ ጽኑ ወዳጅነት ወደ ጠላትነት መቀየር፣ ልጆችን በተለያየ አደጋ ማጣት፣ ክፉ ዘዴኛነት ፣ ብልጠት፣ ራስ ወዳድነት፣ ማታለል አስገራሚ ጭካኔዎች ሲሆኑ፤ ለምን ? እንዴት ማለታችን አልቀረም፡፡ ጌታ  የት ሄዶ ነው ይህ  ሁሉ የሚሆንብን ትሉ ይሆናል፡፡

 የብሉይ ኪዳን የመጨረሻው ነብይ መጥምቁ ዮሐንስ እንዲህ ዓይነት ጥያቄ ተፈጥሮበት ነበረ '' የምትመጣው መሲህ አንተ ነህ  ወይስ ሌላ እንጠብቅ ?'' ብሎ ወደ ኢየሱስ መልዕክተኞችን ላከ፡፡ወንጀል ሳይሰራ እስር ቤት መግባቱ ፣ በዚህም ላይ ብዙ የመሰከረለት ብርቱው ኢየሱስ በርሱ ጉዳይ ጣልቃ ገብቶ ፣ አልያም አንዳች ተዐምራት ሰርቶ እርሱን ከእስር አለማስፈታቱ አደናግሮት ይሆናል፤ ነገር ግን ከዚህም የከፋ ሆነ፡፡ በእስራቱ ጊዜ ዝም ማለቱ ሲገርመን ፡ ጭራሽ በሔሮደስ ልደት ላይ ለዘፈነች አንዲት ወጣት ብላቴና ጥያቄ መሰረት አንገቱ ተቆርጦ በወጪት ቀረበ፡፡ ጌታስ ? ዝም! በቃ ዝም!

     አንዳንዱ ጉዳይ ከእኛ አዕምሮ በላይ ነው፡፡ ምናልባት ከጌታ ጋር መግባባት ስለማንችል ይሆን ዝም የሚለን? እስጢፋኖስን በድንጋይ ወግረው ሲገድሉት ሁሉን የሚችለው ጌታ በዙፋኑ ላይ ቆሞ እያየው ነበር፤ ለምን እንዳላስጣለው አይታወቅም፣ የታመነው ምስክሩ አንቲጳስ ሲገደል ጌታ ጣልቃ አልገባም ፣ ሐዋርያቱ በዘይት ተጠብሰው ሲሞቱ፣ ህዝብ በተሰበሰበበት አናብስት ቦጫጭቀው ሲገድሉዋቸው የጠራቸው ጌታ በዙፋኑ ላይ ነበር፡፡ ለአንዳንዱ ጥያቄ መልስ በእጃችን የለም፡፡ አንድ የእግዚአብሔር ሰው እንዳሉት በፊሊፒንስ የጭቃ ጎርፍ 250 ህጻናትን ለምን ከድኖ እንደገደለ አናውቅም፡፡ በቅርብ ጊዜ አንድ የምታሳሳ ወጣት ከሲያትል ለሚሽን ጉዞ ወደ ህንድ ሄዳ በተመሳሳይ ለአገልግሎት ወደ ኢትዮጵያ የሄደው መጋቢ አባት ከጥቂት ቀናት በሁዋላ ተጠርቶ የመጣው ፡ ልጅህ ድንገት ሞታለች ተብሎ ተረድቶ ነበር፡፡ በጣም አሳዛኝ ነበረ፡፡ በሌላ ጊዜ አንድ  ዘማሪት እህት እናቱዋን በሞት ያጣችው ኦፕራሲዎን ልታስደርጋቸው ወስዳ በወቅቱ ሐኪሞቹ መቀስና ሌሎች ነገሮች ሆዳቸው ውስጥ ረስተው ስለ ሰፉአቸው ነበር፡ ነገሩ ኢንፌክሽን ፈጥሮባቸው ዳግመኛ ሲደረጉ  እንደሞቱ ነው ለቅሶ ስደርስ የነገረችኝ፤

ወገኖች ለእኛ የሚበጀን ወደ እግዚአብሔር መቅረብ ነው ፤ ጥያቄያችን ባይመለስም እናመልከዋለን ፣እንወደዋለን፡፡ እንደዚህ የመሰሉ ቀናትን ልናሸንፍ  / ልንቁዋቁዋም / እንችላለን ፤የምንችለው ግን ፡ የእግዚአብሔርን ዕቃ ጦር በመልበስ  / በማንሳት/ ነው፡፡ መሳሪያው ሰው ሰራሽ  ወይም አሜሪካ ፣ጃፓን ሰራሽ መሳሪያ ሳይሆን የእግዚአብሔር ዕቃ ጦር ይለዋል፡፡ እግዚአብሔር ለዚህ ክፉ ጊዜ እንዲሆነን ያዘጋጀልን መከላከያ እና ማሸነፊያ ዕቃ ጦር ነው፡፡ ቢያንስ ስድስት ነገሮች ናቸው ፤ቀጥለን እናያቸዋለን፡-

1-  የእምነት መታጠቂያ- ወገባችን ላይ

2-  የጽድቅ ጥሩር- ደረታችን አካባቢ

3-  የሰላም ወንጌል- እግሮቻችን ላይ

4-  የእምነት ጋሻ- በአንደኛው እጃችና ላይ

5-  የመዳን ራስ ቁር- በጭንቅላታችን ላይ የሚደረግ

6-  የመንፈስ ሰይፍ /የእግዚአብሔር ቃል ነው/- በቀኝ እጃችን ይዘን የምናጠቃበት ነው፡፡

   ከ ራስ እስከ እግራችን ድረስ መሸፈን ያስፈለገን ምክንያት ጠላት እኛን ለመጉዳት ወይም ለመግደል ከጭንቅላታችን ጀምሮ ወርውሮ ስለሚሞክረን ነው፡፡ መዳኑ አስተማማኝ የሆነን ክርስቲያን ጭንቅላቱን መትቶ ሊጎዳው አይችልም፡፡ ነገር ግን ደረቱን በጥሩር ካልታጠቀ ማለትም ጽድቅ ላይ ገና የሚያመቻምች ሆኖ ካገኘው ይጎዳዋል፡፡ ነገር ግን እርሱም ከተሸፈነበት ቢያንስ እግሩን ስበሩት ብሎ መልዕክተኛ ይልካል:: ይህን ጊዜ ጠንካራ የወንጌል ከስክስ ያላደረገ  ሆኖ ከተገኘ ፡ ባይሞትም እንኩዋ ዘመኑን ሁሉ በመንፈስ እያነከሰ ይኖራል ስለዚህ ሙሉውን ትጥቅ መታጠቅና መመላለስ አለብን፡፡ እንደሚታወቀው ሰይጣን ትንሽ ቀዳዳ ፈልጎ  ነው የሚያጠቃን ፤ያልተሸፈነ አካላችንን ፈትሸን እንልበስ  /እንታጠቅ/፡፡

  የእስራኤል ንጉስ አክዐብ የሞተው በጥሩርና በጥሩር መጋጠሚያ በኩል ከጠላት ወገን በተወረወረ ቀስት ተወግቶ ነው፡፡ ምናልባት ሁሉን ታጥቆ ነበር፤ ይሁንና  መቀነት ግን አላደረገም እንደማለት ነው፡፡ ምንም እንኩዋ በእርሱ ሞት ላይ ፍርድ ከእግዚአብሔር ዘንድ የወጣም ቢሆን፡፡ጥቃት የደረሰበትና ለሞት የበቃው ግን በተገኘው ክፍተት በኩል ነበር፡፡

 ወገኖች ሙሉ የእግዚአብሔርን ትጥቅ ታጥቀን በዚህ ዘመን እንድንኖር አሳስባችሁዋለሁ! እስቲ የላሉትን ጠበቅ እናድርጋቸው፤ ከትናንሽ ጥያቄዎቻችን እንውጣና ኩርፊያውን ትተን በእግዚአብሔር ፊት በጽድቅ ፣ በእውነት እንመላለስ!! የሚመጣልን መድኀኒት እርሱም ክርስቶስ ወደ ልዩ እረፍት ቦታ ይወስደናል፡፡ ብንጸና እንወርሳለን፡፡ በነገር ሁሉ ጌታ ከሁላችን ጋር ይሁን ፡፡ አሜን!!!

ማስታወሻ፡-  ይህ ለቅዱሳን የተዘገጋጀ መልዕክት ነው፡፡

                                                                                                             benjabef @gmail.com                            

Saturday, April 4, 2015

ፋሲካ !

                                ለብርሃነ ትንሳኤው እንኩዋን አደረሳችሁ!

'' ወይቤሉን ፡ አትደንግፃ፡፡ ኢየሱስሃኑ፡ ናዝራዊ፡ተኀሥሡ፡ ዘተሰቅለ፡፡ ተንሥአ፡ ወኢሀሉ፡ ዝየስ፡ ወናሁ፡ መካኑ፡ ኀበ፡ ተቀብረ፡፡ ''
 /እርሱ ግን እንዲህ አላቸው፡ አትደንግጡ፡ የምትፈልጉት የተሰቀለውን የናዝሬቱን ኢየሱስን ነው፡ እርሱ ተነስቶአል፡ እዚህ የለም፡ እርሱን ያኖሩበት ስፍራ ይኸውላችሁ፡፡/ ማርቆስ 16፤6

 ጌታችን ፣ መድኀኒታችን ና አምላካችን  ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ሁላችን በደል እና ሐጢያት መከራን ተቀብሎ በመስቀል ላይ ከሞተ በሁዋላ ፡ በሶስተኛው ቀን ከሞት ተነስቶአል፡፡ ይህ ብርሃነ ትንሳኤው ነው በመላው ዓለም የፋሲካ በዐል ተብሎ  የሚታወቀው ፡፡

ፋሲካ የስሙ ትርጉዋሜ ማለፍ  ማለት ሲሆን፤ ይህም እስራኤላውያን ከ 430 በግብጽ በባርነት አገዛዝ ከነበሩበት አሰጨናቂ ዓመታት ነጻ የወጡበት ቀን ነው፡፡ በዚያም ቀን ምሽት በሁሉ ቤት ታርዶ የነበረው ጠቦት ፣ በበራቸው ጉበንና በመቃናቸው የለቀለቁት ደም ምሳሌነቱ ክርስቶስና የክርስቶስ ደም ነው፡፡ጌታችን እኛን ከሐጢያትና ከኩነኔ ሊያድነን ዋጋ ከፍሎአል፡፡ አሁን በአዲስ ኪዳን ዘመን ከ ዓለም ልንወጣ የምንችለው ደግሞ የአዲስ ኪዳኑን / የፋሲካውን በግ / በማመንና በመቀበል ሲሆን ፣ በቀራኒዮ በፈሰሰው ደሙም ከሚመጣው ቁጣ ማምለጥ እንችላለን፡፡ ደሙን በጉበኑ ባላደረገ ቤት ሁሉ ሞት እንደነበረ፡ በክርስቶስ ደም ያልነጻ እና የደሙ ማህተም በግንባሩ የሌለ ማንኛውም ሰው ከዘላለም ሞትና ፍርድ ማምለጥ አይችልም፡፡

እርሶም ዛሬ ከግብጽ  / ከዓለም / ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ በክርስቶስ አምልጠው አውነተኛውን የክርስትና ህይወት ሊኖሩ የሚወስኑበት ጊዜ እንዲሆን እመኝልዎታለሁ፡፡ በዛሬዋ ቀን በመስቀል ላይ ስለ እርሶ ሞቶ የተነሳውን ጌታ ና መድሓኒት በልብዎ ውስጥ ስፍራ ይስጡት፡፡ እስቲ የቀረዎትን  ዘመን ለሞተውና ለተነሳው ጌታ ሊሰጡት ዛሬ ይወስኑ! እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ይረዳዎታል፡፡

                                                                              መልካም የትንሳኤ በዓል ይሁንልዎ!!!

      


  ማስታወሻ፡-  ይህንን መልዕክት ፋሲካውን እያከበሩ ላሉ ወዳጅ  ዘመዶቻችን ሁሉ ሼር እናድርግ!

                                                                                                          benjabef@gmail.com

orthodox mels kaalaat 3