Saturday, February 21, 2015

የእግዚአብሔር አሳብ !

ወደ ዓለም ሁሉ ሂዱ ፡ ወንጌልንም ለፍጥረት ሁሉ ስበኩ፡፡
 /ወይቤሎሙ፡ ሑሩ፡ ውስተኩሉ፡ ዓለም፡ ወሰብኩ፡ ወንጌል፡ ለኩሉ፡ ፍጥረት፡፡ / ማርቆስ 16፤15፡፡

ወንጌል ለፍጥረት ሁሉ እንዲሰበክ ትዕዛዝ የሰጠን ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ወንጌል መስበክ የአንድ ወቅት ስራ አይደለም፡፡ እኛ ወደ ጌታ እስከምንሔድ ወይም ጌታ በዳግም ምፅዓት እስኪመለስ ድረስ የምንከውነው ታላቅ የሆነ ሰዎችን የማዳን ተገግባር ነው፡፡

አንዳንድ ጊዜ ይኸው ወንጌልን የማሰራጨት ተልዕኮ ለጥቂቶች ብቻ የተተወ  ይመስላል፡፡ ሌሎቹ  ምንም የማይመለከታቸው ነውን? አንዳንድ ጊዜም በዘመቻ ይጀመርና በዘመቻ ሲተውም ይታያል፡፡ በእኔ እምነት አንድ ቤተክርስቲያን ወንጌል መስበኩዋን ማቆም ያለባት በዓለም ውስጥ ያሉ ሰዎች ሁሉ ድነው ካበቁ እና የዓለም ፍጻሜ ደርሶ ጌታ ዳግመኛ ሲመጣ ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ወንጌልን መስበክ ማቆምና እንደፈለግን አጀንዳውን መቀያየር የምንችል አይመስለኝም ፡፡ ቤተክርስቲያንን የመሰረታት እና ራስ የሆነላት ጌታ እስኪመለስ ድረስ አድርጉ ብሎ ያዘዘውን ተልዕኮ መፈጸም ይኖርብናል፡፡ ተቁዋሙ የእርሱ ነውና፤ በቤቱ የእርሱ ትዕዛዝ ሊተገበር እንደሚገባ አስባለሁ ፡፡

 መሰረታዊው  ነገር ይህ ሆኖ ሳለ፡ በሌላ በኩል ደግሞ ወንጌልን በግድ ፣በፍርሀትና በመጨነቅ እንዳንሰብክ ደግሞ ያስፈልጋል፡፡ ታዲያ እንዴት እንስበክ ?... ከውስጥ በሆነ ፍቅር! በጋለ ስሜት! ነፍሳት እንዲድኑ ባለ እውነተኛ ቅንዐት  / passion   /፡፡ በነገራችን ላይ ለወንጌል ብቻ ሳይሆን፡ ሰለ ሌላውም  ስለምናደርገው ነገር አስቀድሞ ፍቅርና መነሳሳት ቢኖረን ጥሩ ነው፡፡ ቶዘር የሚባል አንድ መንፈሳዊ ሰው እንደተነናገረው '' አንድን ነገር ከመስራት በፊት ለዚያ ነገር ፍቅርና መነሳሳት ያሻል፡፡ በእግዚአብሔር መንግስት ውስጥ ትልቁ ነገር፡ ከሌሎች ነገሮች ይልቅ እግዚአብሔርን መውደድ ነው፡፡ የውስጥ መነሳሳት፣ ለነፍሳት የሚኖረን ፍቅር ፣ ተልዕኮና አገልግሎት ሁሉ የሚገኘው ወይም የሚገነባው ለክርስቶስ ኢየሱስ ባለን ጥልቅ ፍቅር ላይ ተመስርቶ ነው '' ብሎአል፡፡

            ከውስጥ የሆነ ፍላጎት /passion/ እንዴት ይመጣል?
ከመጽሐፍ ቅዱስ ላይ ለምሳሌ የነህምያን ታሪክ ብንመለከት፡ ከጦቢያና ሰንበላጥ  የመጣበትን ዛቻ ና ማስፈራሪያ ሳይበግረው ህዝቡን አስተባብሮ የኢየሩሳሌምን ቅጥር በ 52 ቀናት  ሰርቶ የጨረሰ ታላቅ ባለ ራዕይ ነው፡፡ የትልቅ ነገር ባለ ራዕይና ባለ ገድል ከመሆኑ በፊት ግን፡ እስራኤላውያን፡ ተግዘው በሄዱበት በስደት ምድር - በባቢሎን ቤተመንግስት ውስጥ በጠጅ አሳላፊነት ሙያ ተቀጥሮ ኑሮውን ሲገፋ የነበረ ሰው ነው፡፡አንድ ቀን ግን አናኒ የሚባል ወንድሙ ስለ ኢየሩሳሌም ጉዳይ ወሬ ይዞ መጣ፡፡ ያንን ወሬ ሌሎችም  የእስራኤል ሰዎች ሳይሰሙ አይቀርም፡፡ ከሰማው ነገር ተነስቶ አንድ ነገር ለማድረግ የወሰነ ግን አናይም፡፡ ነህምያ ግን የኢየሩሳሌም ቅጥር መፍረስና ፣የአባቶቹ መቃብር ያለበት ከተማ በር መቃጠሉን ሲሰማ  ልቡ ተነካ፤ አያሌ ቀን ተቀመምጦ  አለቀሰ፡፡/ነህ.1፤3-4/፡፡ ይህ ብቻ አይደለም፡ በሰማይ አምላክ ፊት እያዘነ ይጾምና ይጸልይ ነበር፡፡ በዚህ መልክ ውስጡ ሲነካ ነው ፡ወደ ቀጣዩ እንቅስቃሴ የተራመደው፡፡ ከሞቀ ስራው አስፈቅዶ ወጥቶ የሄደው፤ ሌሎችን ሁሉ አስተባብሮ ቅጥሩን ሰርቶ የጨረሰው፡፡

ልክ እንደዚህ የሆነ ነገር ስንሰማ፣ ስንሰበክ፣ ስንማር ወይም  ስናነብ፣ ቅዱስ ቅንዓት ውስጣችን ሊገባ ይችላል፡፡ የወንጌል ቅንዓትም ወይ በዚህ መልኩ አልያም በሌላ መንገድ ውስጣችን ይመጣል፡፡ ለምሳሌ በሉቃስ ወንጌል 15 ላይ የምናገኘውና ክርስቶስ የተናገረውን ምሳሌ እንመልከት፡፡ታሪኩ ባጭሩ እንዲህ ነው፡፤ አንድ ሰው መቶ በጎች ነበሩት ፤ከመቶዎቹ መካከል አንደኛው በግ ወደ በረሀ ኮበለለ፡፡ ወዲያውም ሰውዬው የነበሩትን ዘጠና ዘጠኙን በመተው የጠፋውን አንዱን ሊፈልግ እንደሄደ ይገልጻል፡፡ያሉትን ዘጠና ዘጠኙን ይባርክልኝ ብሎ እንደ መቀመጥ ፡እንዴት ስለ አንድ በግ  ብሎ ፍለጋ ወጣ  ? ብንል፤ መልሱ ሊሆን የሚችለው ስለ አንድ ግድ የሚያሰኝ ጥልቅ ፍቅር ገብቶበት ነው! በጉ ጠፍቶ መተኛት አይችልም፡፡ ቀጥሎም ነገሩን ከልቡ ሆኖ እንደሚያደርገው የሚያሳየን  '' እስኪያገኘው ድረስ  አጥብቆ መፈለጉ ነው፡፡'' ቁ.4 ፡፡ ካገኘው በሁዋላ ደግሞ፡ ደስታውን የገለጠበት መንገድ በተጨማሪ ልቡንና ቅንዐቱን ያሳየናል፡፡ በጫንቃው ተሸክሞ ወደ ቤት አምጥቶ፣ ጎረቤቶቹን ጠርቶ፣ ደስታውን ገለጸ ይላል፡፡ ካደረጉስ ማድረግ እንዲህ ነው፤ እስኪያገኙ ድረስ አጥብቆ መፈለግ !

     ዛሬ በኛ ዘመን ስንት በግ ጠፍቶብን ነው የተቀመጥነው?

እ.ኤ.አ. ሚያዚያ ወር 2012  ላይ ስለ ዓለም ህዝብ ቁጥር  አንድ አለም አቀፍ ሪፖርት ወጥቶ ነበር ፡፡ሪፖርቱ እንደሚያመለክተው በአሁኑ ሰዐት የዓለም ህዝብ ቁጥር 7 ቢሊዮን ገደማ ይሆናል ተብሎ ይታሰባል፡፡ ከዚህ ውስጥ 750 ሚሊዮን ወይም 11% የሚሆነው ህዝብ በኢየሱስ ክርስቶስ አዳኝነት  የሚያምን፣ 2.6 ቢሊዮን የዓለም ህዝብ ወይም  38%  ገደማ የሚሆነው ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ አዳኝነት የሰማ ነገር ግን ያልተቀበለ  / ሌሎች አዳኞች አሉ ብለው የሚያምኑ/ ፣ የተቀረውና ሰፊው ህዝብ ማለትም 3.5 ቢሊዮን ወይም  50% ገደማ የሚሆነው ምንም የወንጌል መልዕክት ያልሰማና የክርስቶስን አዳኝነት ያልተቀበለ ነው፡፡
   ከነበሩት መቶ  በጎች  አንዱ ቢጠፋ አክንፎ ያስኬደው ፍቅር ተጽፎልን ከሶስት  ቢሊዮን በላይ የዓለም ህዝብ ጠፍቶ ምንም ሳይመስለን ተረጋግተን መቀመጣችን  ምን ያህል አዚም ቢደረግብን ነው? ማን ነው ይህን ታላቅ ቅንዐት ከውስጣችን የዘረፈብን? እርግጥ ነው በዚህ የተቀደሰ ተግባር ላይ የተሰለፉ ተግዳሮቶች በርካታ ናቸው፡፡ ውስብስብም ናቸው፡፡ ነገር ግን ጌታ ተልዕኮውን በሰጠበት ጊዜ " አይዞአችሁ እኔ  እሰከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ከእናንተ ጋር ነኝ ብሎናል '' ማቴ.28፤20፤

ነፍሳትን ከሲኦል የመታደግ አገልግሎት በእግዚአብሔር መንግስት ካሉት አገልግሎቶች ሁሉ ላቅ ያለው ነው፡፡ ነገር ግን ደግሞ ከላይ እንደተገለጸው ትልቅ ውጊያ ያለበት አገልግሎት ነው፡፡ በስጦታ ካልሆነ በቀር ብዙዎች በምርጫ ደረጃ ላይመርጡት ይችላሉ፡፡ ምክንያቱም ብዙ መስዋዕትነትን የሚጠይቅ በመሆኑ ነው፡፡ ይሁንና ታላቅ የነፍስ እርካታ የሚገኘውም ፡ የነፍስ ማዳን ርብርቦሽ ውስጥ እንደሆነስ  ያውቃሉ? ሰው  ከሲኦል ሲያመልጥ ያለ እርካታ!

 ወንጌልን መመስከር ከልባችን ተነክተን እንድናደርገው፡ ነፍሳትን የመታደግ ቅንዓት እንዲጨምርብን አስቀድመን ብንጸልይ መልካም ነው፡፡ ፍሬያማ ና ውጤታማ እንድንሆን ያግዛልና፡፡ ብንጸልይ ሊሰጠን እንደሚችል ከተጻፈልን ተስፋ ቃሎች ውስጥ ሁለቱን እንመልከት፡-

1-  ማቴዎስ  ወንጌል 7፤7-8 '' ለምኑ ይሰጣችሁአል፤ፈልጉ ታገኙማላችሁ፤ መዝጊያን አንኩዋኩ  ይከፈትላችሁዋል፡፡ የሚለምነው ሁሉ ይቀበላልና፣ የሚፈልገውም ያገኛል፤ መዝጊያንም ለሚያንኩዋካ ይከፈትለታል፡፡'' እንደሚል፤ ከልባችን እየፈለግን እንለምን፡፡ በሩን እስኪከፍትና እስኪሰጠን  ድረስ  ደጋግመን በሩን እንቆርቁር፡፡ በተስፋ ቃሉ መሰረት በሩን ይከፍትልናል፡፡ ሌሎችን የምናተርፍበት የወንጌል ቅንዐት ከብዙ ጥበብ ጋር ወደ ልባችን ይገባል፡፡

2-  ሁለተኛው የያዕቆብ መልዕክት 1፤17 ላይ ነው ያለው፡፡ እንዲህ ይላል፡-'' በጎ ስጦታ ሁሉ ፍጹምም በረከት ሁሉ ከላይ ናቸው ፤መለወጥም በእርሱ ዘንድ ከሌለ በመዞርም የተደረገ ጥላ በእርሱ ዘንድ ከሌለ ከብርሃናት አባት ይወርዳሉ፡፡''  ለወንጌል  የመቅናት ስጦታ በጎም ፍጹምም ነው፡፡ ይህን በረከት ከጌታ ልንቀበል እንደምንችል ቃሉ ያሳያል፡፡

ፀሎት፡- ጌታ ሆይ  የወንጌልን ቅናት እንድትሰጠን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እለምንሀለሁ፡፡  
       
               አሁን ለኛ ቀን ነው ሌሊት?
'' ቀን ሳለ የላከኝን ስራ ላደርግ  ይገባኛል፡፡ማንም ሊሰራ   የማይችልባት ሌሊት ትመጣለች፡፡'' ዮሐ.9፤4፡፡
    በሰው ህይወት ውስጥ ቀንም ሌሊትም አለ፡፡ ይህ ሁሉን ሰው ሲያጋጥም የኖረ፣ የሚኖር ጉዳይ ነው፡፡የምንሰራበት ምቹ ጊዜና ሁኔታ ይሰጠናል ፤ደግሞ ሌላ ጊዜ መስራት ብንፈልግና ጊዜ ቢኖረን እንኩዋ የወደድነውን ማድረግ የማንችልበት ሌሊት ደግሞ ይመጣል፡፡የተመቻቸው ቀን ላይ ያልሰራ፣ያልተጋ ሰው የማይሰራበት ሌሊት ሲመጣበት ይቆጨዋል፡፡
     ከወንጌል መስበክ አኩዋያ እነዚህን ሁለት ሁነቶች በምድራችን ላይ እንኩዋ ማሰብ ይቻላል፡፡ አንዱ  ወንጌልን በነጻነት መስበክና ማስተማር የማይቻልበት  ጊዜ ነበር፡፡ ምናልባት ደግሞ አሁን በአንጻራዊ  ሁኔታ ቤተክርስቲያን በድብብቆሽ  ከምትሰበሰብበትና ከምትሰራበት ሁኔታ ወጥታ ወንጌልን በትልልቅ  አዳራሾች ና በአደባባይ መስበክ ችላለች፡፡ ይህ ሲባል ግን መቼም ዘመን ቢሆን ወንጌልን ከመስበክ ጎን ለጎን ከሚገጥሙ ትንሽም፣ ትልቅም  ተግዳሮቶች ጋር ማለት ነው፡፡
  ይሁንና ይህንን ነጻነት ተጠቅመን የማንሰብክበት፣ የማንመሰክርበት ከሆነ ነገ ደግሞ ሌሊት ሊመጣብን ይችላል፡፡ ቀጥሎ ምን እንደሚከሰት አይታወቅም፤ የወንጌል ተቃዋሚዎች በዓለም ላይ ከመቼውም ጊዜ ይልቅ አይለው ተነስተዋል ጌታም ለጊዜው ስለ ፈቀደላቸው ይመስለኛል፡ አንዳንድ በጸሎት መከልከል የማንችላቸውን ድርጊቶች ሁሉ እያደረጉ ያሉበት ጊዜ ላይ ነን፡፡ ነገ በእኛ አካባቢ ምን ሊከሰት ይችላል?  ከህግ ፣ከዲሞክራሲ አንጻር የሰው መብት አትንካ ፣የራስህን አመለካከት ሰው ላይ መጫን አትችልም፤ የስብከት ፍቃድ፣ የአገልጋይነት ፍቃድ....ወዘተ የሚሉ ነገሮች ከአሁኑ በራችንን እያነኩዋኩ ነው፡፡ ለምሳሌ  የኤርትራ ወንድሞችና በዚያም ያለች ቤተክርስቲያን ሌሊት ውስጥ ናቸው ያሉት፡፡ እንደሚሰማው መስበክ ና መናገር አይቻልም፡፡ ደግሞ እግዚአብሔር ምናልባት በቅርብ ጊዜ ምቹ ቀን ይሰጣቸዋል፡፡ ከዚህ ሀዘናቸውም ይጽናናሉ ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ይሁንና እኛ ግን ከእንደነዚህ  አይነት ሁኔታዎች መማር አለብን እላለሁ፡፡
   
            ወንጌልን በራሳችን ዘመን ...!
" ዳዊት በራሱ  ዘመን  የእግዚአብሔርን  ሐሳብ  ካገለገለ  በሁዋላ  አንቀላፋ፡፡" ሥራ.13፤35
 ዳዊት በተሰጠው በራሱ ዘመን እንዲሰራው የተቀመጠለትን ነገር አድርጎ ማለፉን ነው ቅዱስ ሉቃስ የዘገበልን፡፡አሁን እኛ በእኛ ዘመን እንድንሰራው የሚፈለግ ታላቅ የእግዚአብሔር ዓላማ፡ በዋነኛነት ምን ሊሆን ይችላል?  ይህንን ጥያቄ  ለመመለስ  በሚደረጉ ጥረቶች ብዙ ሰዎች የተለያየ በጎም የሚመስሉ፣  በጎም ያልሆኑ አመለካከቶች ውስጥ ገብተዋል፡፡ ፊት ለፊት የተቀመጠላቸውን የእግዚአብሔርን አጀንዳ ችላ ብለው ሲመራመሩ ፡አላስፈላጊ ወደ  ሆኑና ከእግዚአብሔር የልብ ትርታ ጋር ግንኙነት ወደሌላቸው ፣ ከአንድነት ይልቅ መከፋፈልን፣ ከትህትና ይልቅ ትዕቢትን ፣ለሌላው ከማሰብ ይልቅ ለራስ ብቻ በሚያደላ አፍቅሮ ነዋይ እየተሳቡ ገብተው ሲለፉና ሲሰቃዩ ማየት የተለመደ ነገር  ሆኑዋል፡፡ሁሉም ድርጊቶች የሚፈጸሙት በእግዚአብሔር የዘመኑ አሳብ ፣ ራዕይ ና ጥሪ ስም ነው፡፡ በተለይም  ቤተክርስቲያን  ዋና ነገሩዋን ስትስት ከማየት በላይ የሚያም ምን ነገር አለ? እግዚአብሔር ግን በዚህ ዘመን ማድረግ የፈለገውን አሳቡን በግልጽ ተናግሩዋል '' በክርስቶስ ለማድረግ እንደ ወደደ እንደ አሳቡ የፍቃዱን ሚስጥር አስታውቆናልና፡፡'' በዘመን ፍጻሜ ይደረግ ዘንድ ያለው አሳቡም በሰማይና በምድር ያለውን በክርስቶስ ለመጠቀቅለል ነው''  ኤፌ.1፤10፡፡ ሁሉም በኢየሱስ ክርስቶስ ውስጥ እንዲሆንና ለእርሱም እንዲሆን ባለ የመለኮት አጀንዳ ውስጥ ተሳታፊ መሆን  ምን ያህል ታላቅ ዕድል ነው?! ሰዎችን ሁሉ በክርስቶስ  የምናደርግበት መንገዱ ደግሞ ወንጌልና ወንጌል ብቻ ነው፡፡ ለሰው  የሞኝነት መንገድ የሚመስል በእግዚአብሔር ዘንድ ግን አስቀድሞ የታሰበ ዘዴ ፣ጥበብ ፣ ብልሀት ነው፡፡ '' ....ያለ ሰባኪስ እንዴት ይሰማሉ፣ ካልሰሙስ እንዴት ያምናሉ? ''----የተባለበት ሚስጥር፡፡
               
             ቤተክርስቲያን ሆይ ንቂ !
  ጾምና ጸሎት ይዘን በወንጌል ሳይሆን በተለያዩ ዘመነኛ ሃጢያቶች ና ሱሶች ቀስ በቀስ እየተወረሰ  ያለውን ህብረተሰብና አካባቢ እንዲሰጠን መጸለይ ብንጀምርስ ? ክፉ በብዙ እየተጋ ነው፡፡ ከቤተክርስቲያን በሰበብ አስባብ የጸሎት ቀናት ፣ሰዐታት እያስቀነሰ ፣የማለዳ  ጸሎቶች ፣ አዳር ጸሎቶችን እያስተወ፡ ያለምንም ውጊያ እየሰራ ያለ ይመስላል፡፡ መሳሪያዎቹዋን ቀስ በቀስ የተዘረፈችዋ ቤተክርስቲያን በአሁኑ ሰዐት መንቃት ይጠበቅባታል፡፡ ሙሽራው ሊመጣ በደጅ ነው እያልን ሙሽሪት ተገቢውን ልብስ  ሳታደርግ ፣ሳትዘጋጅ እንዴት ይሆናል?
  ቤተክርስቲያን ትውልዱን እየተናጠቀች  ካልጸለየች ሌላ የተጋ ይወስዳቸዋል፡፡ ዲያቢሎስ ለራሱ አጀንዳ እንደሚጸልይ  የእግዚአብሔር ቃል ይናገራል፡፡ እንዲህ ይላል፡- '' ሰይጣን እንደ  ስንዴ  ሊያበጠጥራችሁ ለመነ" ሉቃ.22፤31 ፡፡ የሰይጣን ልመና ትውልድን የማበጠር፣ የማድከምና የመበተን ሲሆን : ጌታ ግን ስለ ጴጥሮስ '' እኔ ግን እምነትህ እንዳይጠፋ ስለ አንተ አማለድሁ '' ይላል፡፡ምንም እንኩዋ ጴጥሮስ በፈተናው ተሸንፎ ክዶ ሄዶ የነበረ ቢሆንም ቆይቶ በንስሀ ተመልሱዋል፡፡ ለመመለሱ ምክንያት የነበረው ግን ጌታ ስለ እርሱ ስለ ማለደለት ነው፡፡/ቁ.32/
     ቤተክርስቲያን ዕቅድ ያላወጣችበትን ህዝብ እና ስፍራ ጠላት እያቀደበት ነው ፡፡ ሰሞኑን አይ ኤስ የተባለው እስላማዊ ድርጅት ምን እየደረገ እንደሆነ ለማንም ጆሮ ባዳ አይደለም፡፡ የደከሙ መንግስታትን እያሰሰ ይቆጣጠራል ፣ ይደራጃል፤ ለምሳሌ ጋዳፊ የወደቁበት ሊቢያ፣ ሳዳም ሁሴን የወደቁበት ኢራቅ፣ በብዙ ጦርነት የደቀቀችውን ሶሪያ....እንደ የመን ያሉ ሌሎችንም አገሮች፡፡ በትንሽ ተዋረድ ደግሞ ወንጌል ለመስበክ ያላሰብንባቸው አካባቢዎች ና ጠንካራ ጸሎት የማይደረግባቸው ልል ቦታዎች ልክ ጠንካራ መንግስት እንደሌለባቸው አገሮች ለክፉው ስራ የተጋለጡ  ይሆናሉ፡፡ ለምሳሌ ምን ምን ያልነበረባቸው አንዳንድ አካባቢዎች  እንደ ወረርሽኝ የጫትና የተለያዩ አደንዛዥ ዕጾች ማከፋፈያ እና መጠቀሚያ ሆነው ሲታዩ ፤የዝሙት ማስፋፊያ፣ የመጠጥ ንግድ ቤቶች ፣ዳንኪራ ቤቶች እንደ ሰደድ እሳት በየቦታው በፍጥነት ሲስፋፉ፡ ከሁዋላ  ደጀን የሆናቸው ና ዕቅድ አውጪው  ማን ነው?  በዚህ ሁሉ ቤተክርስቲያን የት ነች? ለትውልዱ ምን እያሰበች ነው?

በዚህና  በዚያ ተወጥሮ  ያለውን  ወጣት ትውልድ  ከጠላት  መንጋጋ  ለማላቀቅ  ተግቶ  እየጸለየ ያለ ማን ነው? የትውልድ  ሸክም ያለበት የዘመኑ  የወንጌል ሰው ማን ነው? ቀድማ አይታ  የተነሳች ፣ እንደ ሰራዊት  እየጸለየች ያለች  የዘመንዋ  ቤተክርስቲያን  የቱዋ ነች?  ለሚከፈቱ  አጥቢያዎች አጀንዳ  ያላት፣ ለወንጌል በጀት ያላለቀባት፣ የጌታ  ዋነኛ  አሳብ  የገባት  አጥቢያ  የት ናት? ሲመስለኝ ሰይጣን የቤት ስራ ሰጥቶን ፡እርሱ የራሱን ስራ እየሰራ ነው፡፡ አንገብጋቢና ዋና  ባልሆኑ ነገሮች ላይ ጊዜ እንድንፈጅ ፣ እርስ በርስ እንድንለያይ፣ ወንድም ወንድሙን እንዲጠላ ፣ቤተክርስቲያን  ከቤተክርስቲያን ፣መሪዎች ከመሪዎች  እንዲራራቁና እንዳይግባቡ ተደርገናል፡፡ እንደ ጥንቱዋ ቤተክርስቲያን መሪዎች ስለ ተሐድሶ ወይም ስለ ሪቫይቫል ሊያስቡ በሚገባበት ጊዜ ላይ '' የማርያም አይን ጥቁር ነው ቡናማ ?''፣ '' በአንድ መርፌ ላይ ስንት መላዕክት ይቆማሉ?''፣ '' ቅዱስ ቁርባን ውስጥ ዝንብ ብትገባ ዝንቡዋ ትቀደሳለች ወይስ ቁርባኑ ይረክሳል ? '' በሚሉ ጭቅጭቆች ተወጥረው፣  በሐሳብ ተለያይተው፡ ውድ ጊዜያቸውን እንዳቃጠሉ ፤ ሰይጣንም ኑፋቄዎችን በቤተክርስቲያን አሾልኮ ለማስገባት ዕድል እንዳገኘ፡ ዘንድሮም ታሪክ ራሱን እንዳይደግም ብናስተውል መልካም ነው፡፡
   ሩቅ የመሰሉን ነውሮች ቤተክርስቲያን ደጅ ላይ፣ ብቻ አይደለም ምስባኩ ላይ ከወጡ ቆዩ፤ የጺዮንን በር የተዳፈሩ ጆሮን ጭው የሚያደርጉ በርካታ ነገሮች  እየሆኑ ነው ፡፡ እኛስ እንደ ዳነ ሰው ፣ እንደ ቤተክርስቲያን  ምን እያሰብን ነው?

በመጨረሻ፡- ቢቻል የቤተክርስቲያን መሪዎች እና የሚመለከታቸው ሁሉ ተሰብስበው አዳዲስ  የወንጌል ምስክርነት ዕቅድ ቢያወጡ ፣
                  -ጥቂት በእግዚአብሔር ፊት ጊዜ እንዲወስዱና እንዲሰሙት ቢሆን መልካም ነው፡፡
                - በማንኛውም የወንጌል ዕቅዶች ላይ ለመመካከር ከፈለጉ  በሚከተለው አድራሻ  ይጻፉ E-mail ‹ benjabef@gmail.com ›

ማሳሰቢያ ፡- ይህንን መልዕክት የቤተክርስቲያን መሪዎች ለሆኑ ሁሉ እንዲደርስ ያድርጉ!!! ሃላፊነታችንን በጋራ እንወጣ!!!

Friday, February 20, 2015

አማላጅነት-2

             ክፍል -2

በዚህ በክፍል ሁለት ትምህርት ውስጥ ካለፈው የቀጠለውንና ከዚህ ሐሳብ ጋር ተያያዥነት ያላቸውን ጥያቄዎች እናነሳለን፡፡
  • ሐጢያትን  ለካህን  መናዘዝ  ተገቢ  ነውን ?
  • የአዲስ ኪዳን  ዘመን  ካህናት  እና ሊቀ  ካህን  ማን ነው?
  •  በጻድቃን  ስም  ቀዝቃዛ  ውሀ  ማጠጣት  ያጸድቃል?
  •  ዝክር  መዘከርና  ምጽዋት  ማድረግ  ለጽድቅ  ይጠቅማል?
  • የሙታን  ተስካር  ወይም  /ፑርጋቶሪ/ ምንድን  ነው?
                  የአዲስ ኪዳን  ካህናት እነማን ናቸው?
        ስለ ካህናት ስናነሳ በቅድሚያ መታወቅ ያለበት ጉዳይ፡ ካህናት በብሉይ ኪዳን የነበራቸው ሚና እና የአዲስ ኪዳን ክህነት ምን እንደሆነ ነው፡፡ የብሉይ ኪዳን ካህናት የሚመረጡት ከሌዊ ነገድ ሲሆን ምግባራቸውም የቤተ መቅደሱን መንፈሳዊ ስርዐት መምራት ነው፡፡ በተለይም ለኀጢያት ስርየት የሚቀርቡ መባ ና መስዋዕቶችን ህዝቡን ወክለው በእግዚአብሄር ፊት የሚያቀርቡት እነርሱ ነበሩ፡፡ የብሉይ ኪዳን ህዝብ ሐጢያቱን የሚናዘዘው የሚሰዋው በግ ወይም ጠቦት ላይ ሲሆን ሊቀ ካህኑም ደሙን ይዞ በአመት አንድ ጊዜ ወደ ቅድስተ ቅዱሳን ይገባል፡፡/ ዕብ.9፤6-7 /

  በአዲስ ኪዳን ዘመን ለሐጢያት ተብሎ የሚቀርብ መስዋዕት ወይም ደም የለም፡፡ሊቀ ካህናችን የሆነው ጌታችን መድሐኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የገዛ ደሙን ይዞ ወደ እውነተኛው የሰማይ መቅደስ እንደገባ መጽሐፍ ቅዱስ ይናገራል፡፡/ዕብ.10፤11-18/ በአሁኑ ሰዐት እስራኤላውያን፣ ካህናቱ ሌዋውያንን ጨምሮ በተወሰነ መንገድ ስርዐቱን የሚከተሉ ቢሆንም የእውነተኛውን አዳኝ የኢየሱስ ክርስቶስን ትንሳኤ ና ጌትነት ግን አልተቀበሉም፡፡

               የማሰርና የመፍታት ስልጣን...!
        የማሰርና የመፍታት ስልጣን የተሰጣቸው ካህናት እነማን ናቸው? በማቴዎስ ወንጌል ም.18 ቁ.18 ላይ እንደተጠቀሰው "...እውነት እላችሁዋለሁ በምድር የምታስሩት ሁሉ በሰማይ የታሰረ ይሆናል፤በምድርም የምትፈቱት ሁሉ በሰማይ የተፈታ ይሆናል፡፡":: በሌላም ስፍራ  ጌታ ለጴጥሮስ እንደተናገረው " የመንግስተ ሰማያትንም መክፈቻዎች እሰጥሀለሁ በምድር የምታስረው ሁሉ በሰማይ የታሰረ ይሆናል፤በምድርም የምትፈታው ሁሉ በሰማያት የተፈታ ይሆናል" ማቴ.16፤18፡ አንባቢ  እንደሚረዳው እነዚህ ቃላት የተነገሩት የመጀመሪያው ጥቅስ የጌታችን ደቀመዛሙርት ለነበሩት ለመጀመሪያዎቹ የበጉ ሐዋርያት ሲሆን፤ ሁለተኛው ደግሞ ለሊቀ ሐዋርያው ለጴጥሮስ የተነገረ ነው፡፡መሰረታዊውን ታሪክ ለማስታወስ ብዬ ነው እንጂ፤ በሌላ ዘመን ለሌሎች ክርስቲያኖች ቃሉ አይሰራም ለማለት አይደለም፡፡ ሁሉም የአዲስ ኪዳን ሰዎች ናቸው፤ በክርሰቶስ በመሲሁ አዳኝነት ያመኑ እስራኤላውያን ናቸው፤ ደግሞ የክርስቶስ ሞቱና ትንሳኤው ምስክር ለመሆን የተመረጡ ወንጌል ሰባኪዎች  ናቸው፡፡ ለእነርሱ ግን የተለየ ልብስ እና የተለየ ጥምጥም አልነበራቸውም፡፡
     ሁለቱም ሐሳብ የብሉይ ኪዳንን ስርዐት ስለሚከተሉ ካህናት አይናገርም፡፡ ለእነርሱ እንዲህ ያለ ስልጣን የላቸውም፡፡ እንደዚህ ለመሆን አስቀድሞ በክርስቶስ በኩል ከእግዚአብሔር ጋር መታረቅ ነበረባቸው፡፡
     ከዚህ ጋር በተያያዘ ኢየሱስ ያንን ለምጻም ከፈወሰ በሁዋላ " ሄደህ ራስህን ለካህን አሳይ !" ሉቃ.5፤14 ያለውስ ጉዳይ ? ብለን ብናነሳ፡ በቅድሚያ ጌታችን መድሐኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመጣበት ጊዜ በምድር ላይ የነበረው ስርዐት የአይሁድ ስርዐት እንደመሆኑ ሙሉ ለሙሉ ስራውን ፈጽሞ አዲስ ኪዳንን እስኪተካ ድረስ የሙሴን  ህግ በመታዘዝ ነው ይህንን ያደረገው፡፡ አንደኛ ህግን ልሽር ሳይሆን ልፈጽም ነው የመጣሁት ስላለ ማቴ. 5፤17፡፡ ሁለተኛው በዘመኑ የነበሩ ፈሪሳውያን ሙሴን ህግ ይሽራል የሚል ተደጋጋሚ ክስ ቢያነሱም፡ እርሱ ግን ያንን አለማድረጉን ካሳየበት አንዱ ማሳያ ይህ ታሪክ ነው፡፡በሙሴ ህግ እንደተቀመጠው ሰው በለምጹ ከሰፈር ከተወገደ በሁዋላ ሌላ ጊዜ በሆነው መንገድ ቢፈወስ ወደ ህብረተሰቡ ከመቀላቀሉ በፊት ራሱን ለዘመኑ ካህናት ማሳየት ነበረበት፡፡ካህኑም መንጻቱን አረጋግጦ ወደ ሰፈር ይቀላቅለው ነበር፡ ዘሌዋውያን 14፤2-32፡፡ ስለዚህም ጌታ የፈወሰውን ያንን ለምጻም በህጉ መሰረት በካህናቱ እንዲታይ ነው የሰደደው፡፡ ያንንም ያደረገው በትህትናና በታዛዥነቱ ነው፡፡ በዚህም ላይ የነጻን ለምጽ ሄዶ ለካህናት ማስፈተሸ ሐጢያትን ለእነርሱ ከመናዘዝ ጋር ምን ግንኙነት አለው? በዘመኑ የብሉይ ኪዳን ካህናት ከለምጹ የነጻን ሰው የሚፈትሹት እነርሱ ነበሩና ያንን አደረገ፡፡ከህጉ በላይ የሚቀኑለትን ወግና ስርዐታቸውን ግን አጥብቆ ይኮነንን ነበር፡ /ማር.7፤14-21/
     የአዲስ ኪዳን ዘመን ህዝብ ሐጢያቱን መናዘዝ ያለበት በኢየሱስ ክርስቶስ ስም በኩል  በቀጥታ ለእግዚአብሔር ነው፡፡ የአዲስ ኪዳን ሊቀ ካህንና መካከለኛ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ዕብ.9፤15፡፡ በእርሱ የሚያምኑ ሁሉ ደግሞ ካህናት ተብለው ተጠርተዋል፡፡!1ጴጥ.2፡9 ፡፡በዚ መሰረት አንዱ ስለ አንዱ እርስ በእርስ ሊጸልይ ይችላል እንጂ፤ ለብቻው የተለየ ልብስ የለበሰ እና ለእርሱ ብቻ የሚገባ የጸሎት መጽሐፍ እያነበበ ንስሐ የሚያድል እና የህዝብን ሐጢያት የሚያስተሰርይ ሰዋዊ የክህነት ስርዐት የለም፡፡እግዚአብሔር  ሁሉንም ሰው በአንድ ጊዜ መስማት ስለሚችል፤ በፊቱ ንስሀ የሚገቡትን ሁሉ በክርስቶስ ይቅር ይላቸዋል፡፡ 1ዮሐ.1፡4-9፣ሥራ.10፤48፡፡

             በጻድቅ ስም ውሀ  የሚያጠጣ .. !?
" እናንተን የሚቀበል እኔን ይቀበላል፤እኔንም የሚቀበል የላከኝን ይቀበላል፡፡ ነቢይን በነቢይ ስም የሚቀበል የነቢይን ዋጋ ይወስዳል፤ጻድቅንም በጻድቅ ስም የሚቀበል የጻድቅን ዋጋ ይወስዳል፡፡ማንም  ከእነዚህ  ከታናናሾቹ ለአንዱ  ቀዝቃዛ  ጽዋ ውሀ  ብቻ  በደቀ መዝሙሩ ስም የሚያጠጣ አውነት እላችሁአለሁ ዋጋው አይጠፋበትም፡፡ " ማቴ.10፤40-42፡፡
 በጥሞና አንድ ጥያቄ እናንሳ የነቢያትና የጻድቃን ዋጋቸው ምንድን ነው?  ነቢይ እግዚአብሄርን ሰምቶ ላመጣው መልዕክት፡ ዋጋው ሰው ሲመለስ ፣ንስሀ ሲገባ ማየት ፣ከመቅሰፍት ከዕልቂት አምልጦ በፈንታው ለእግዚአብሔር እየተገዛ ሲኖር ማየት ነው፡፡ ጻድቅም አመጻን ጠልቶ  በጽድቅ ለኖረበት ኑሮ ጌታ የሚከፍለው መንፈሳዊና ስጋዊ በረከት ነው፡፡ ስለ መንግስተ ሰማይ ስለ መግባት ጉዳይማ ቢሆን ማንም ቢሆን በህግ እና በስራ አይድንም /ኤፌ.2፤8-9/፡፡ ከዚህ ጋር ሌላው ዋና ነገር  " እናንተን የሚቀበል እኔን ይቀበላል " የሚለው ቃል ነው፡፡ ጻድቃንን ስንቀበል የምንቀበለው እነርሱ የሚሰብኩትን መድሐኒታችንን ኢየሱስን ነው፡፡ እርሱ እነርሱን ያዳነና ያጸደቀ በመሆኑ ልክ እነርሱን ተቀብለን ስናስተናግድ፣ ስንሰማቸው ፡ስበኩ ብሎ የላካቸውን ጌታ እንቀበላለን፡፡ ጻድቃንን የተቀበላችሁ ወገኖቼ  መስክሩ ብሎ የላካቸውን ኢየሱስንስ ተቀብላችሁዋል?? እርሱ እናንተን  የሚቀበል እኔን ይቀበላል ብሎአልና፡፡  በደቀ መዝሙሩ ስም ቀዝቃዛ ውሀ  የሚያጠጡ ሰዎችም ዋጋቸው አይጠፋም! ነው  እንጂ  የሚለው  አጸድቃቸዋለሁ አይደለም፡፡ ዋጋው /ክፍያው/ ብዙ ዓይነት ነገር ሊሆን ይችላል፡፡ለዘላለም ህይወት መንገዱ ግን አንድ ብቻ ነው፡፡ እርሱም ሰው በሆነው በክርስቶስ አምኖ ንስሐ መግባት ነው፡፡/ዮሐ.14፤6/፡፡

  አያይዘን ዝክርን፣ ምጽዋትን፣ ሌሎች ለጽድቅ ተብለው የሚደረጉትን ነገሮች ሁሉ ብንመለከት እንዴት መንግስተ ሰማይ ለመግባት ሊጠቅሙን ይችላሉ?  በእንደዚህ ሁኔታ መዳን ቢቻል ኖሮ ለምን መድኀኒዓለም መጥቶ ዋጋ  ከፈለልን ? ለምን ተገረፈ ?፣ ተሰቀለ ?፣ ሞተ ?፣ ተቀበረ ? ለምን ?? ቃሉ የሚለን  " ነገር ግን ሰው በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን አንዲጸድቅ እንጂ በሕግ ስራ እንዳይሆን ስጋን የለበሰ ሁሉ በህግ ስራ ስለ ማይጸድቅ እኛ ራሳችን...እንጸድቅ ዘንድ በክርስቶስ ኢየሱስ አምነናል፡፡ ገላ.2፤16፡፡ በሐዋርያት ሥራ 4 ቁ.12 ላይ እንደተገለጠውም ወአልቦ፡ ካልእ፡ ሕይወት፡ ወአልቦ፡ ካልእ፡ ስም፡ በታሕተ፡ ሰማይ፡ ዘይትወሀብ፡ ለእጉዋለ፡ እመሕያው፡ በዘ፡ የሐዩ፡፡ /መዳን በሌላ በማንም የለም፡እንድንበት ዘንድ የሚገባን ለሰዎች የተሰጠ  ስም ከሰማይ በታች ሌላ የለምና፡፡"

   ቆርነሌዎስ የሚባለው ሰው / በሐዋርያት ስራ ምዕራፍ 10፤1-48 ላይ የምናገኘው/ ፡ ለጽድቅ ብሎ ብዙ ነገሮችን ይፈጽም ነበር፤ ለምሳሌ ይጾም ነበር፣ ከቤተሰዎቹ ጋር እግዚአብሔርን የሚፈራና የሚያመልክ ነበር፣ ለድሆች እጅግ ምጽዋት ያደርግ  ነበር፡፡ ምንም እንኩዋ ድርጊቱ ደስ የሚያሰኝና እግዚአብሔር ዘንድ የደረሰም ቢሆን ለመጽደቅ ግን ዋነኞች ጉዳይ ስላልነበሩ፡ መልዐክ  ወደ እርሱ ዘንድ ተልኮ ስለ ክርስቶስ ወንጌል የሚነግረው፣ እንዲያምን የሚረዳውና የሚያስተምረው ደቀመዝሙር ጠቁሞት ልኮ አስመጥቶታል፡፡ ያደረገው ነገር ሁሉ ለመዳኑ በቂ  ከነበረ  ጴጥሮስ ለምን ወንጌል እንዲነግረው ታዘዘ ?  መልካም ስራዎች ሁሉ በጌታ ያመኑና የጸደቁ ሰዎች ሊያደርጉት የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡ በመልካም ስራቸው ጌታቸውን ማስመሰገንና መግለጥ ስላለባቸው፡፡ በጎ ስራ መስራት ዝክር፣ ጾምና ጸሎት፣ ምጽዋት ማድረግ ግን ብቻውን አያጸድቅም፡፡

              የሙታን ተስካር
  ለሞቱ ሰዎች መጸለይ ይገባል! የሚሉ ሰዎች መነሻ ጥቅሳቸው 2ኛ መቃቢያን 12፡41-46 / ከ66ቱ መጽሐፍ ቅዱስ ውጪ ባለ አዋልድ መጽሐፍ ላይ የሚገኝ/ ሲሆን፤ በእርገግጥ በጥንት ጊዜ ጀምሮ በቻይናውያን እምነትም ዘንድ እንደ ቡዲዝም ባሉት እምነቶች ሙታንን ወክለው መስዋዕት ማቅረብ የተለመደ ነገር ነው፡፡
 ለሙታን መጸለይ /ፑርጋቶሪ/ አንድ ሰው ከሞተ በሁዋላ ነፍሱ ሲኦል ትገባለች፤ ነገር ግን ቤተሰቦቹና ዘመድ አዝማድ ከሞተበት ዕለት ጀምሮ እስከ ሰባት ዓመት ድረስ በየተወሰነው ጊዜ በስሙ ዝክር ቢያወጡለት ቀስ በቀስ ከሲኦል እየወጣ ይመጣና በሂደት ገነት ይገባል የሚል የኑፋቄ ትምህርት ነው፡፡ ምናልባት ወደፊት የምናነሳቸው የገድላት መጽሐፍት ለዚህ ትምህርት አስተዋጽኦ አድርገዋል ብዬ አስባለሁ፡፡

  1.   ነገር ግን ሉቃስ 16 ቁ.19-31 ከቀረበውና ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተናገረው ምሳሌ እውነቱን  መማር እንችላለን፡ አንድ ሰው የሆነውን ሆኖ ከሞተ ወዲያ ሰማይ ላይ ሔዶ የሚያስቀይረው ሐሳብ የለም፡፡ በጻድቃን ሰማዕታት ምልጃና ልመናም መዳን አይችልም፡፡ ክፍሉ ላይ እንደተመለከተው ሐብታሙ ሰው ከሲኦል ሆኖ ምንም አብርሐምን በእሳት እየተንገበገበ ቢለምንም '' በዚህ ያሉ ማለትም በአብርሐም እቅፍ ውስጥ በእረፍት ያሉ ወደ ስቃዩ ስፍራ መሄድና ማዳን እንዳይችሉ በመካከል ታላቅ ገደብ ተደርጎአል:: '' ነው ያለው፡፡ / በገነት ያሉ ወደ ሲኦል ፤በሲኦል ያሉ ወደ ገነት መምጣት አይችሉም ! / ፡፡ ከዚያ በሁኣላ በምድር ላይ አባቱ  ቤት ስላሉ 5ት ወንድሞቹ  ነው የተጨነቀው፡፡ ወደዚህ ስቃይ ስፍራ እንዳይመጡ ሰው ከሞት ተነስቶ ይመስክርላቸው ብሎ ተማጸነ፡፡ ምናልባት እንደርሱ ሰማይ ስንሔድ ጻድቃን ሰማዕታት አሉልን! ብለው ተዘናግተው ከሆነ እንኩዋ፤እውነቱ ያ እንዳልሆነ ስለተረዳ ይሆን ?  ለማንኛውም ለዚህም ጥያቄ ቢሆን እዛው ምድር ላይ ያሉትን መስካሪዎች /ሙሴና ኤልያስ አሉላቸው / እነርሱን  ይስሙ ነው የተባለው፡፡ ተመለከታችሁ በሰማይ ምንም አይነት ቀልድ እንደሌለ? ሐጢያተኛ ሰው ከሞተ ወዲያ፡ ፍርድ ብቻ ነው የሚጠብቀው፤ አንድ  ጊዜ  በፍርድ  ሲኦል  የገባን   ነፍስ  ተከራክሮ ፣ ውሳኔ  አስቀይሮ  ወደ ገነት ሊያመጣ  የሚችል  አንድም  መልዐክ  ወይም  ጻድቅ  የለም!!!   ወገኖቼ አንሞኝ ዛሬውኑ ፡ቀን ሳለልን ፣ትንፋሻችን ሳይቆም በክርስቶስ አምነን እንዳን ! አውነተኛ ንስሐም እንግባ፡፡ ጌታ ሆይ ሐጢያቴን ይቅር በለኝ ልጅህን ኢየሱስን የህይወቴ አዳኝ አድርጌ እቀበላለሁ እንበል፡፡ አሁኑኑ ባሉበት ቦታ ሆነው ንስሐ ሊገቡ ይችላሉ፡፡

ማስታወሻ፡- በተጨማሪ አማላጅነት ክፍል- 1ን  ያንብቡ፣ ለዘመዶችዎ እና ለወዳጆችዎ ሁሉ ይላኩላቸው! ይጸልዩላቸው!  

                                                                  benjabef@gmail.com


Monday, February 16, 2015

ንገስባት!

                                           ከፍል-1

 በመጽሐፍ ቅዱስ  ላይ ስለ ሐጢያት በርካታ ቦታዎች ላይ ተጠቅሱአል፡፡ ብዙ የእግዚአብሔር ሰዎች በብርታትም ፣በድካምም አልፈዋል፡፡ ሁሉም ነገር ለትምህርታችን የተጻፈ ነው፡፡ ዛሬ በዚህ ርዕስ ስር የተወሰኑትን በማንሳት በሐጢያት ላይ መንገስ መጽሐፍ  እንዴት እንደሚያስተምረን እናያለን፡፡

        ሐጢያት ምንድን ነው?

1-  የመጀመሪያው ሐጢያት ያለመታዘዝ ነው፡፡ ዘፍ .3፤11
2-  ሐጢያት ቶሎ የሚከብ ነገር ነው፡፡ ዕብ.12፤2
3-  በደጅ /በልብ/ የሚያደባ ነገር ነው፡፡ ዘፍ.4፤7
4- ዕድል ካገኘ በስጋ ላይ መንገስ የሚችል ነው፡፡ሮሜ 8፤12

ሐጢያትን ልክ እንደ ኮምፒውተር ቫይረስ ውሰዱትና፤ ቫይረስ እንዴት በስርዐት የተቀመጡትን ፕሮግራሞች እንደሚያዛባ፤መረጃዎችን እንዴት እንደሚያጠፋ፤እንዲሁም የተለመደውን ስራ እንዳይሰራ እንዴት እንደሚያስተጉዋጉል መመልከት ይቻላል፡፡ሐጢያትም  ልክ እንደዚሁ በሰው ውስጥ ያሉትን በጎ ራዕይና ዓላማዎች እንዳይሳኩ የሚያደናቅፍ ፣ ሰውን ከአምላኩ የሚለይ፣ከራሱ የተፈጥሮ ሁኔታ አስወጥቶ ሌላ ፍጡር የሚያስመስል፤ እንዲሁም ሰዎች ለሰዎች  ካላቸው  የተቀደሰ ህብረትና ግንኙነት የሚለይና የማበላሸት አቅምን የሚጨምር ነው፡፡ ዛሬ ዛሬ ክርስቶስን ከዙፋን አስወርዶ ወደ ምድር ያመጣውን፣ ታላቅም የህይወት ዋጋን ያስከፈለው ሐጢያት እንደቀላል በማየት በህይወታቸው ዕቃቃ የሚጫወቱ ብዙዎች ናቸው፡፡ለኀጢያት ዝቅተኛ ግምት የሚሰጥ ክርስቲያን ኀጢያት ምን እንዳስከፈለ በትክክል አልተረዳም እንደ ማለት ነው፡፡

ቫይረስ በአንቲ ቫይረስ እንዲጠፋ እንዲሁ የሐጢያት ማስወገጃው የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ክቡር ደሙ ነው፡፡ምክንያቱም የፈሰሰው በትክክል ለሐጢያታችን ማስተሰርያ በመሆኑ ነው፡፡ምናልባት አንቲ ቫይረሶች እንደየ ሁኔታው ሊለያዩ ቢችሉም፡ አንዳንድ ጊዜ አንዱ አንዱን ማጥፋት ላይችል ይችላል፡፡ ዓለም ላይ ለተሰራው ማንኛውም ሐጢያት በሙሉ ግን መንጻት የሚቻለው በክርስቶስ ደም ብቻ ነው፡፡ለሐጢያት ሌላ ተስተካካይ ክፍያ የለውም ወይም የትኛውም ሀይማኖታዊ ና በጎ ተግባራት ለበደል መቀነሻነት /ማስተሰረያነት/ ሊውሉ አይችሉም፡፡ይህ የክርስቶስን ደም ማቃለል ነው የሚሆነው፡፡

ታዲያ በሀጢያት ላይ መንገስ የምንችለው እንዴት ነው? ከዚህ በፊት እሰቲ የሐጢያት ምንጩ ከየት እንደሆነ እንመልከት......ማርቆስ ወንጌል ም.7 ቁ.20 እስከ 23 ላይ ሲናገር  እንዲህ ይላል " ከሰው የሚወጣው ሰውን የሚያረክስ ያ ነው፡፡ከውስጥ ከሰው ልብ የሚወጣ ክፉ ሐሳብ፣ዝሙት፣ መስረቅ፣መግደል፣ ምንዝርነት፣ መጎምጀት፣ ክፋት፣ ተንኮል፣ መዳራት፣ ምቀኝነት፣ ስድብ፣ ትዕቢት፣ ስንፍና ናቸው፤ይህ ክፉው ሁሉ ከውስጥ ይወጣል፡ ሰውንም ያረክሰዋል፡፡" በዚህ መሰረት ሐጢያት ከውጪ የሚመጣ ነገር ሳይሆን ከውስጥ ያለ ግፊት ነው ማለት ነው፡፡ ልክ ነው፡፡ ለምሳሌ አንድ ሰው ከመስረቁ ወይም ዝሙትን ከመፈጸሙ በፊት ልቡ ውስጥ ያስባል፡፡ዝሙትና ስርቆቱ ድርጊቶቹ እና ፍጻሜዎቹ ናቸው፤ እንጂ ቀድሞም ቢሆን በልብ ፣በሐሳብ ሳይጨረስ ወደ ድርጊት አይገባም፡፡አንድ ሰው ሰኞ ላይ ሆኖ ቅዳሜ ስለሚፈጽመው ሐጢያት ሊያስብ ይችላል፡፡ ሐጠጢየያተቱ ሰኘኞ ጀምሮአል እንጂ ገና ቅዳሜ አይደለም የሚጀምረው፡፡አሁን ርብርቦሹ የተደረጉ ሐጢያቶች ላይ ሆኑዋል፡፡ ነገር ግን ጥራትና ጽዳት የሚያስፈልገው ምቹ ቀናትና ሁኔታን እየጠበቀ ያለ ውስጣዊ ሐጢያት ላይ ነው፡፡ እዚህ ውስጥ ታዲያ የሰይጣን ተሳትፎው ምንድን ነው? ካልን ክፉ ሐሳብ መላክ፣ ሁኔታዎችን ማመቻቸት..ወዘተ ነው ፡፡እንጂ የማንንም እጅ ይዞ ና ጠምዝዞ ሐጢያት አያሰራም፡፡ ሔዋንንም ቢሆን በቃልና በሐሳብ ነው የማረካት ድርጊቱን ያደረገችው እርስዋ ነች፡፡

          የሐሳብ መበላሸት

   ለሰው ልጆች ሁሉ ውድቀት ሰበብ  የሆነው  የህይዋን  ስህተት የመጣው ሰይጣን ሐሳቡዋን አበላሽቶት ነው፡፡ 2ቆሮ.11፤3 ፡፡ ሐሳቡ የተበለላሸበት ሰው ወደ ድርጊቱ ለመግባት ቀላል ይሆንለታል፤ ልክ እንደ ቃየን ሁሉ የዳዊት ልጅ አቤሴሎምም ወንድሙን አምኖንን ከመግደሉ በፊት ረጅምና የቆየ የግድያ ሐሳብ አርግዞ ነበር፡፡ ጊዜውና ሁኔታዎች ሲመቻቹለት ደግሞ አስገደለው፡፡ 2ሳሙ.13፤2፡፡

   አንዳንድ ጊዜ ክፉ ሐሳብ ያድርና ድርጊቱ ሊቆይ ይችላል፤ ይህን ጊዜ መንቃት ነው፡፡ ምንም እስካላደረኩ ድረስ ንጹህ ነኝ  ማለት አይቻልም፡፡ ቀን የሚጠብቅ ክፉ ምኞት ላይ መንገስ ያስፈልጋል፡፤ እግዚአብሔር ቃኤልን ቀድሞ ያስጠነቀቀው ለዚያ ነው፡፡ ደጅህ ላይ ሐጢያት እያደባች ነው ንገስባት አለው፡፡ አለዚያ እርሱዋ  ትነግስብሃለች፡፡ ያን ጊዜ ፍቃዱዋን ታደርጋለች፡፡እግዚአብሄር ወደ ቃየን መጥቶ ከነገረው ነገር የምንማረው ኀጢያት ላይ እኛ መንገስ ካልቻልን ኀጢያት በእኛ ላይ መንገስ ይጀምራል፡/ ዘፍ.4፤7/የሚለውን ነው፡፡

   ያዕቆብ 1፤15 ላይ ሲናገር '' ምኞት  ጸንሳ  ሐጢያትን  ትወልዳለች ፡ሐጢያትም  ጸንሳ  ሞትን ትወልዳለች፡፡ " ሞት የሚባለው /ውድቀት ሊሆን ይችላል/፤ ከመከሰቱ በፊት ውስጥን ይዞ  የሚከርመው ሐሳብ  /ምኞት/ ነው፡፡ ምኞት ዝም ከተባለ ቆይቶ ቆይቶ  ሀጢያትን ይወልዳል፡፤ ከዚያም ወደ ሞት ያመጣል፤ ሁሉም ሂደት ነው ማለት ነው፡፡ ሐጢያትን፣ሞትንና ውድቀትን በህይወቱ ማየት የማይፈልግ ሰው ራሱን ማንጻት ያለበት ከውስጥ ነው፡፡ ምን አርግዣለሁ? ብሎ ራስን መጠየቅ፡፡ የአስቆሮቱ ይሁዳ ጌታን አሳልፎ እንዲሰጥ በቅድሚያ ሐሳብ ነው የመጣበት፡፡ '' ዲያቢሎስም ሐሳብ ካስገባ በሁአላ ''ይላል፡ ምናልባት ዲያቢሎስ ወደ አዕምሮው የላከበትን ሐሳብ መቃወም ይችል ነበር ፡፡ ምናልባትም ወደ ሌሎች ደቀመዛሙርትም ሐሳብ ቀርቦም ይሆናል፡፡ ምናልባትም እነርሱ ተቃውመውት ይሆናል፡፡ ይሁዳ ግን ሐሳቡን አስተናገደ፤ ወደ ቀጣዩ ና ከባዱ ነገርም አለፈ፡፡ ሮሜ 6፤12 ''...ለምኞቱ እንድትታዘዙ በሚሞት ስጋችሁ ሐጢያት አይንገስ '' ስጋችን ላይ ሐጢያት ሲነግስ  እንደ ስጋ ፈቃድ ለመኖር የስጋን ነገር አዘውትረን እንድናስብ እንገደዳለን፡፡ /ሮሜ.8፤5/

   ውስጡ የተሸነፈን ሰው ወደተገዛለት ነገር በቀላሉ መጎተት ይቻላል፡፡ ብዙ የሚያቅተው ከነገሮች ውስጥ መውጣት ሳይሆን ነገሮችን ከውስጥ ማስወጣት ነው፡፡ እስራኤላውያን በእግራቸው ከግብጽ ውስጥ ወጥተው ነበር፡ ነገር ግን በቆይታ እንደታየው ግብጽ ውስጣቸው ነበረ፡፡ ስለዚህም በልባቸው ወደ ግብጽ ተመለሱ ይለናል፡፡/ሥራ.7፤39/፡፡ ከዓለም ወጥተን ግን ዓለም ውስጣችን ካለች  እየዘመርን ፣ እየጸለይን ፣ ቤተክርስቲያን እየሄድን የሐጢያት ተጠቂዎች ልንሆን እንችላለን፡፡ ከሁሉ ነገር ተገልለው አንድፊቱኑ ገዳም ለገቡ መነኮሳት እንኩዋ ትልቁ  ትግል የውሰጥ ነው፡፡ ከግብጽ ወጥተህ ግብጽ ግን ከልብህ ካልወጣ ችግር ነው፡፡የሎጥ ሚስት  ከሶዶም በእግሩዋ ወጥታለች ነገር ግን ሶዶም ከውስጥዋ አልወጣም ነበርና እንቅፋት ሆነባት፡፡ መቀየር ፣መለወጥ  ከውስጥ ነው፡፡ ለዚህም ነው የእግዚአብሔር ቃል በአዕምሮአችሁ መታደስ ተለወጡ እንጂ ይህን ዓለም አትምሰሉ......" የሚለን፡፡ ከየ ዕለቱ ኑሮአችን እንኩዋ ብንመለከት አንድ ሰው ወተት ወይም ጎመን የሚጠላ ቢሆን፡ ከፈለገ  ቦታ ቢመጣም ወይም ነጻም ቢሆን አይነካውም፡፡ ሐጢያትን ከውስጥ ስንጠላ አዩኝ አላዩኝ ከሚል መሳቀቅ እንወጣለን፡፡ በዚህም ላይ ውስጣችንን ቦርቡሮ በጊዜ ሒደት ከሚጥለን ነገር እንገላገላለን፡፡ ልክ እንደ ጎመኑ ና ወተቱ  የትም ብንሆን ፣መቼም ቢሆን አንነካውም፡፡

አንድ የእግዚአብሔር ሰው ሲናገር ውስጡ ችግር ያለበት  ሰው ያማረ  ህንጻ ውስጥ ወይም አውሮፕላን ውስጥ ቢገባ  ችግሩ አያቆምም ብሎአል፡፡ የገባበት ቦታ ነገሩን ሊለውጥ ስለማይችል ነው፡፡ ከዚህ በፊት አንድ በጣም ወፍራምና ዕድሜ ጠገብ ዋርካ አውቃለሁ፡፡ነገር ግን በሆነ ወቅት እምብዛም ነፋስ ባልነበረበት ጊዜ ነው ሌሊት ላይ ወድቆ የተገኘው ፤በጊዜው ሁኔታው ሲጠና ዛፉ በከፍተኛ ሁኔታ ውስጡ በብል ተቦርቡሮ ነበር፡፡ ለረጅም ጊዜ ቅርፊት ተሸፍኖ ያለ እየመሰለ ኖረ፤ነገር ግን ባልታሰበ ቀን ወድቆ ተገኘ፡፡ ብዙ ነገሮች እንደዚያ ይመስሉኛል ተሸፍነን ጠንካራ ሰዎች እንመስላለን፣ አስተማማኝ እና የመላዕክት ህይወት ያላቸው እንመስላለን፤ ምናልባት ውስጣችን ግን በብዙ እየተገዘገዘ ይሆናል፡፡ አሁን አሁን በየ አደባባዩ ላይ የሚሰሙት ውድቀቶቻችንም የዚህ ውጤት ይሆናል፡፡እስቲ  ሁላችንም ውስጣችንን እንፈትሽ ና ነጻ እንውጣ ፡፡ ውድቀትን ብዙ ሰው ሊያየው ፣ ሊሰማው ይችላል፡፡ ከዚያ በፊት ያለን የውስጥ መቦርቦርና ትናንሽ ልምምዶች ግን እምብዛም አይታይም፡፡እኛው ከጌታ ጋር እንፍታው፡፡ልምምዱ ከፍ ያለ ደረጃ እንኩዋ የደረሰ ቢሆን በጾም ጸሎት በፊቱ ብንሆን የማይለወጥ ነገር ምንም የለም፡፡ ጌታ ሁሉን ይችላልና፡፡

ውስጣችን ያለውን፣ የምንቸገርበትን ነገር  በምን እንደምናውቅና ፣ የውስጥን ትግል እንዴት ማሸነፍ እንደሚቻል በክፍል ሁለት ትምህርታችን እንቀጥላለን፡፡

ማስታወሻ:- ይህን ትምህርት ቅዱሳን እንዲጠቀሙበት ያድርጉ፡፡

                                                                        benjabef@gmail.com

Monday, February 9, 2015

ምስጢረ ድነት




    ''ወይቤ፡ መጽሐፍ፡ ኩሉ፡ ዘየአምን፡ ቦቱ፡ የሐዩ " ሮሜ.10፡11
      

       በክርስትና ውስጥ ሊታወቁ የሚገባቸው ትክክለኛ የደህንነት /ድነት/ መሰረቶች እና ሊመለሱ የሚገባቸው ጥያቄዎች የሚከተሉት ናቸው፡-
 በቅድሚያ ድነት የምንለው የነፍስ ድነትን ነው፡፡ ይኸውም ሰው በሐጢያተኝነቱ ሊቀበለው ካለ ፍርድና ኩነኔ አምልጦ በክርስቶስ የዘላለም ህይወትን ስለ ሚወርስበት ጉዳይ ነው፡፡

1- ሁሉም ሰው ሐጢያትን ሰርቶአል?

" ልዩነት የለምና ሁሉ ኃጢያትን ሰርተዋልና የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል፤በኢየሱስ  ክርስቶስ በሆነው ቤዛነት እንዲያው በጸጋው ይጸድቃሉ፡፡"  በግዕዙ እንዲህ ይላል / ወኢፈለጣ፡ ወኢሌ ለየ፡፡እስመ፡ ኩሉሙ፡ አበሱ፡ወጌጋዩ፡ ወኀደጉ፡ ስብሐተ :እግዚአብሔር /   ሮሜ 3፤23       
 " ልዩነት የለም" የሚለው ቃል የሰውን ስጋ ለብሶ ከመጣው ከጌታችን በስተቀር ስጋን የለበሰን ሁሉ ሰው ማለት ነው፡፡ የሐጢያት መንስኤውም አንድም የአዳም አለመታዘዝ ሲሆን / ሮሜ .5፤19/ :ቀጥሎም ሰው ሁሉ በነፍስ ወከፍ ያደረገው ሐጢያት ነው፡፡

2- የሐጢያት ደሞዝ  ምንድን ነው?

" የኀጢያት ደሞዝ ሞት ነውና ::የእግዚአብሔር የጸጋ ስጦታ ግን በክርስቶስ ኢየሱስ የዘላለም ህይወት ነው፡፡" ሮሜ.6፤20 : ጢይት ልክ  እንደማንኛውም ስራ የራሱ ደሞዝ አለው፡፡ ክፍያው ከበድ ያለ ስለሆነም ነው ንስሀ መግባት አስፈላጊ የሆነው፡፡ የኃጢያት ደሞዝ የዘላለም ሞት ነው፡፡ ነገር ግን ከዚህ የዘላለም ሞት ሊታደገን  ፡እግዚአብሔር አንድያ ልጁን ለእኛ ሰጠን /ዮሐ.3፤16/፡፡

3- ከሞት ፍርድ እንዴት  ማምለጥ ይቻላል?

የዮሐንስ ወንጌል ም.3 ቁ 16-18 ሲናገር " በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ህይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ  ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና ፤ዓለም በልጁ እንዲድን ነው እንጂ በዓለም እንዲፈርድ እግዚአብሔር ወደ ዓለም አላከውምና፡ በእርሱ በሚያምን አይፈረድበትም፤ በማያምን ግን በአንዱ  በእግዚአብሔር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን ተፈርዶበታል፡፡ " ከላይ እንደተጠቀሰው  ከዘላለም ፍርድ ና ከዘላለም ሞት ለመዳን መንገዱ በክርስቶስ ማመን ነው፡፡ 

4- መዳን ወይም መጽደቅ  በእምነት ነው፡፡

 የእግዚአብሔር ቃል በሮሜ 10 ቁ.9 ሲናገር / እምከመ፡ ተአምን፡ በአፉከ፡ከመ፡ክርስቶስ፡ውእቱ፡እግዚእ፡ወተአምን፡ በልብከ፡ከመ፡አንሥኦ፡ እግዚአብሄር እምውታን፡ተሐዩ፡፡ወልብን፡ ዘየአምን፡ቦቱ፡ይጸድቅ፡ወአፍኒ፡ዘየአምን፡ቦቱ፡የሐዩ፡፡ " ኢየሱስ ጌታ እንደሆነ በአፍህ ብትመሰክር እግዚአብሔርም ከሙታን እንዳነሳው በልብህ ብታምን ትድናለህና፤ሰው በልቡ አምኖ ይጸድቃልና በአፉም መስክሮ ይድናልና፡፡ መጽሐፍ በእርሱ የሚያምን አያፍርም ይላልና፤" ሮሜ.10፤9-11፡፡ በቃሉ እንደተጠቀሰው የክርስቶስን ጌትነት በአፍ መመስከርና፣ ተሰቅሎ ለኃጢያት ስረየት የሚሆነውን ደሙን አፍስሶ፣ ሞቶ፣ ተቀብሮ፣ በሶስተኛው ቀን ከሙታን ተለይቶ እንደተነሳ ማመን ደግሞ ሁለተኛው ዋና ነገር ነው፡፡

5- ንስሐ መግባት!

 ኢየሱስም ራሱ " ተነስሑ እስመ ቀርበት መንግስተ ሰማያት"- /መንግስተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ ፡፡/ ወንጌል ዘማቴዎስ 4፤17፡፡ በሌላም በኩል ማመንና ንስሐ መግባት የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ናቸው፡፡ በ ሌላ አነጋገር ንስሐ መግባትና ማመን የማይነጣጠሉ ናቸው ማለት ነው፡፡ ታዲያ ንስሐ ስንገባ ኃጢያታችን ይቅር እንደሚባል ተስፋ ተሰጥቶናል፡፡ " በኃጢያታችን ብንናዘዝ  ኃጢያታችንን ይቅር ሊለን ከአመጻም ሁሉ ሊያነጻን የታመነና ጻድቅ ነው፡፡ኃጢያትን አላደረግንም ብንል ሀሰተኛ እናደርገዋለን፡፡ቃሉም በእኛ ውስጥ የለም፡፡ " / 1ዮሐ.1፤9-10/፡፡ መናዘዝ ማለት በስውርና በግልጽ፤ በስህተትና በድፍረት የሰሩትን ሐጢያት ለእግዚአብሔር ዘርዝሮ መናገር ማለት ነው፡፡

6- ጌታን መቀበል ምንድን ነው?

 ጌታን መቀበል የሚለው ቃል የመጣው ከዮሐንስ  ወንጌል ም.1 ቁ.11-13 ባለው  መሰረት ነው፡፡ " ወለእለስ፡ ተወክፍዎ፡ወሀቦሙ፡ሥልጣን፡ውሉደ፡ እግዚአብሔር፡ ይኩኑ ለእለ፡አምኑ፡በስሙ፡፡ " /የእርሱ ወደ ሆነው መጣ የገዛ ወገኖቹም አልተቀበሉትም ፡፡ለተቀበሉት ሁሉ ግን በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ስልጣንን ሰጣቸው፡/ ይላል፡፡ ጌታችን  መድሀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የምንቀበለው  /የምናስተናግደው /  የልባችንን በር በመክፈት ሲሆን በህይወታችን ላይ እርሱን እንደ ሊቀ ካህን፣ እንደ ነቢይ  የዘላለም ጌታና  ንጉስ አድርጎ መሾም ነው፡፡ራዕይ 3፤20

7- ዳግም መወለድ ማለት ምንድን ነው?

   ከላይ የዘረዘርናቸውን መንፈሳዊ እውነቶች በህይወቱ  በመታዘዝ ያደረገ ሁሉ ዳግመኛ ተወለደ ማለት ይቻላል፡፡ በዮሐንስ  ወንጌል ም.3 ቁ.3 እንደሚናገረው  " ኢየሱስ ወይቤሉ፡አማን፡አማን፡እብለከ፡ዘኢተወልደ፡ዳገመ፡አይክል፡ርዕዮታ ለመንግሥተ፡ እግዚአብሔር፡፡" /...እውነት እውነት እልሀለሁ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግስት ሊያይ አይችልም ! ማለት ነው ትርጉሙ::

ለምሳሌ በዚህ ታሪክ ላይ የምናገኘው ኒቆዲሞስ  ሽማግሌ ነበር፣ የአይሁድ አስተማሪ ነበር፣ ይህ ብቻ አይደለም አጥባቂ ፈሪሳዊ  ነበር፣ ደግሞ የአይሁድ አለቃ ነበር፡፡ ረጅም ዘመን ብሉይ ኪዳንን ያስተማረ እንኩዋ ቢሆን፣ ወይም አለቃና በእድሜው የበሰለ የሚባል ሰው ቢሆን?  ዳግመኛ  ካልተወለድክ፤ የእግዚአብሔርን መንግስት አታይም ነው የተባለው፡፡ ስለዚህ ዳግም ሳንወለድ የምናደርጋቸው የትኞቹም ኀይማኖታዊ  እንቅስቃሴዎች  ለመዳናችን  ፋይዳ  የላቸውም:: አንተ ወንድሜ፣ አንቺስ እህቴ  ዳግመኛ ተወልዳችሁአል?

7- ንስሐ  ለገቡ ፣ ዳግመኛ ለተወለዱ  የተዘጋጁ  በረከቶች:-

  •  የዘላለም ህይወት ያገኛሉ፡፡ ዮሐ.3፤18፣ 1ዮሐ.1፡13
  •  ስማቸው   በህይወት  መዝገብ  ላይ ይጻፋል፡፡ ሉቃ.10፤20 ና ራዕይ 20፤15
  •   ከድቅድቅ  ጨለማ ወደሚደነቅ  ብርሀን  ይወጣሉ፡፡1ጴጥ.2፤9
  •  
  •   የክርስቶስ  ክብር  ተካፋይ  ይሆናሉ፡፡2ተሰ.2፤1
  • አዲስ   ፍጥረት ይሆናሉ፡፡ 2ቆሮ.5፤17
  •   ይጸድቃሉ፤  ይድናሉ ፡፡ ሮሜ.10፤ 9፣ ዮሐ.3፤16-18
  •   የእግዚአብሄርም ቤተሰብ ይሆናሉ፡፡ ኤፌ.2፤19፣ 1ዮሐ.5፤1


                                                 benjabef@gmail.com    

Friday, February 6, 2015

አስቸኩዋይ መልዕክት

     "ኢየሱስ ይሰብክ ወይበል፡ተነስሑ እስመ ቀርበት መንግስተ ሰማያት!" ወንጌል ዘማቴዎስ 4፤17           /ኢየሱስም መንግስተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ እያለ ይሰብክ ጀመረ /

                     ለምወዳችሁ  ቤተሰቦቼና ወዳጆቼ

በቅድሚያ የፍቅርና የከበረ ሰላምታዬን  በእግዚአብሔር ስም አቀርብላችሁዋለሁ፡፡ የጌታ ሰላምም ይብዛላችሁ፡፡

ዛሬ ይህንን አጭር መልዕክት ልጽፍላችሁ ያነሳሳኝ ምክንያት ከዚህ በፊት በተደጋጋሚ እንደሰማችሁት በክርስቶስ የማያምኑ ሁሉ የዘላለም ፍርድ ይጠብቃቸዋል ፤ያመኑት ግን የዘላለም ህይወትን አግኝተው መንግስቱን ይወርሳሉ፡፡ስለሆነም ይህንን እውነት ለምወዳቸው ሁሉ አስረግጦ መናገር በዚህ  የመጨረሻ መጨረሻ ጊዜ አስፈላጊ በመሆኑ ነው፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ሰው ልጆች ሁሉ ሐጢያት ሞተ፣ተቀበረ፣በሶስተኛውም ቀን ከሙታን ተለይቶ ተነሳ፤ሞትንም ድል አድርጎ በተነሳ  በ40ኛው ቀን ወደ ሰማይ አረገ፣በአባቱም ቀኝ ተቀመጠ፡፡አሁን በቅርብ ተመልሶ ለፍርድ ይመጣል ፡፡ያን ጊዜም የዓለም መጨረሻው ይሆናል፡፡ ማንም ሰው ይህንን እውነት ቢያምንና ቢቀበል ከዘላለም ፍርድ ያመልጣል፡፡

መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚነግረን  ''ወይቤሉ ኢየሱስ አነ ውእቱ ፍናትኂ ወጽድቅ ወህይወት ወአልቦ ዘይመጽእ ኀበ አብ ዘእበለ እንተ ኃቤየ "  / ኢየሱስም እኔ መንገድና እውነት ህይወትም ነኝ፡፡በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም::/ ብሉዋል፡፡ የዮሐንስ ወንጌል 14፤6፡፡ ይህም የሰው ልጆች ሁሉ ወደ እግዚአብሔር መንግስት ሊመጡ የሚችሉበት እውነተኛና ብቸኛ መንገድ ክርስቶስ እንደሆነ በግልጥ ተቀምጡዋል፡፡

እንዲሁም በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 3 ቁጥር 16-18  " በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ህይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ  ዓለሙን እንዲሁ ወዱዋልና፤ ዓለም በልጁ እንዲድን ነው እንጂ በዓለም እንዲፈርድ እግዚአብሔር ወደ ዓለም አላከውምና፤በእርሱ በሚያምን አይፈረድበትም በማያምን ግን በአንዱ በእግዚአብሐር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን ተፈርዶበታል፡፡" ተብሎ ተጽፉዋል፡፡

ዋና ዋና ነጥቦቹ ፡-  1ኛ- ለሰው ልጆች ሁሉ መዳን እግዚአብሔር አንድያ ልጁን ሰጥቱዋል፡፡

             2ኛ- ክርስቶስ የመጣው ዓለምን ሁሉ ለማዳን ነው፡፡

             3ኛ- በክርስቶስ የሚያምኑ ሁሉ አይፈረድባቸውም፡፡

             4ኛ- በክርስቶስ አምነው ያልዳኑ ሁሉ ፍርድ ይጠብቃቸዋል፡፡ ስለሆነም ከልጅነት እስከ ዕውቀት በማናቸውም ሁኔታ የሰራነውን ሐጢያትና በደል ለእርሱ እየተናዘዝን ለሐጢያታችን የከፈለልንን ዋጋ ማመን አለብን፡፡ 1ዮሐ.1፤9 ሲናገር  "ኀጢያታችንን ብንናዘዝ ኀጢያታችንን ይቅር ሊለን ከአመጻም ሁሉ ሊያነጻን የታመነና ጻድቅ ነው፡፡"

እንግዲህ አንድ ሰው በተሰጠው የዕድሜ ዘመን ሁሉ አንድ ቀንም ይህንን ሳይቀበል፣ኀጢያቱንም ለክርስቶስ ዘርዝሮ ሳይናገርና ምህረትን ሳይቀበል፣ ከዚህ ዓለም በሞት ቢለይ፤ ወይም ክርስቶስ በዳግም ምጽአቱ  ድንገት ቢመጣ ፤የዘላለም ሞት ነው የሚፈረድበት፡፡ የዮሐንስ ራዕይ 20፤15

እናንተም ወዳጆቼ ከዚህ የዘላለም ጥፋትና ስቃይ እንድትድኑ ይህንን የመዳን ወንጌል ቸል ልትሉት አይገባም፡፡

እስኪ ከዚህ በታች ያለውን የንስሐ ጸሎት ከልባችሁ ሆናችሁ ጸልዩ፡- " ጌታ ሆይ እኛ ኃጢያተኞች ነን፤ከልጅነት ጀምሮ እስከዚህ ቀን ድረስ ባለማወቅና በድፍረት የሰራነውን ኃጢያት ሁሉ

 ይቅር በለን፡፡ጌታ ኢየሱስ  ሆይ  ስለ እኛ ሐጢያት መከራን እንደተቀበልክ ፣ደምህን እንዳፈሰስክ ና
 
እንደሞትክልን እናምናለን፡፡ ስለ ሐጢያታችን በፈሰሰው ደምህ ከበደላችን ሁሉ አንጻን ፤ልጆችህም

 አድርገን፡፡ ከዛሬዋ ዕለት ጀምረን አንተን  የህይወታችን ጌታና አዳኝ አድርገን 

ተቀብለንሐል፡፡በልባችንም ላይ ንገስ! ስማችንንም በህይወት መዝገብ ላይ ፃፍልን በኢየሱስ 

ክርስቶስ  ስም አሜን፡፡"

       ይህንን ታላቅ የንስሐ ጸሎት ከጸለያችሁ በሁዋላ ባደረጋችሁት ውሳኔ ፅኑ! በእምነታችሁም እንዳትደክሙ መፅሐፍ ቅዱስን በየዕለቱ አንብቡ፤ ዘውትርም ጸልዩ፡፡ ህይወታችሁን የሰጣችሁት ጌታ በነገር ሁሉ ከእናንተ ጋር ይሆናል፤ይረዳችሁማል፡፡አሜን፡፡

ማስታወሻ፡- እባክዎ እርሶ የተጠቀሙበትን መልዕክት ቢያንስ ለ10 ወዳጆችዎ ይላኩ!!!

 በወንጌል እንደተባለው  " ወቀርበ ኢየሱስ ወተናገርሙ እንዘ ይብል ተውህበ ሊተ ኩሉ ኩነኔ ሰማይ ወምድር ሑሩ መህሩ ኩሉ አሕዛብ እንዘ ታጠምቅዎሙ በስመ አብ ፡ወወልድ ፡ወመንፈስ ቅዱስ ወመሀርወሙ ኩሉ ያዕቀቡ ዘአዘዝኩክሙ፡ወናሁ አነ ምስሌክሙ በኩሉ መዋዕል እስከ ኀልቀተ ዓለም "  /ኢየሱስም ቀረበና እንዲህ ብሎ ተናገራቸው ስልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰጠኝ ፡፡እንግዲህ ሂዱና አህዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችሁአቸው ያዘዝሁዋችሁን እንዲጠብቁ  እያስተማራችሁአቸው ደቀ መዛሙርት አድርጉዋቸው ፤እነሆም እኔ እስከ ኣለም ፍጻሜ ድረስ ሁል ጊዜ ከእናንተ ጋር ነኝ፡፡/  ማቴዎስ 28፤18-20