Saturday, May 7, 2016

ስለ አማላጅነት

የጻድቃን አማላጀነት ያስፈልጋል ወይ ?

የመላዕክት ድርሻስ ምንድን ነው ? የሚሉትን ነገሮች በስፋት እንዳስሳለን፡፡

በቅድሚያ ጻድቅ የሚባለው ማን ነው?  ምን ያደረገ ነው?  የሚለውን መሰረታዊ ጥያቄ መጽሀፍ ቅዱስ ላይ ተመስርተን እንመልስ፡ ጻድቅ ማለት በእግዚአብሔር ፊት ትክክል የሆነ ፣ተቀባይነትን ያገኘ ማለት ሲሆን፡፡ ህግጋትን በመፈጸምና አንድም ሀጢያት ባለመፈጸም የታወቀው ብቸኛ ሰው የሆነው ደግሞ ክርስቶስ ብቻ ነው፡፡ ሌሎች ሰዎች ሁሉ በደልን እንደሰሩ ቃሉ እንዲህ ይላል፡ ‹‹ልዩነት የለምና ሰዎች ሁሉ ኃጢያትን ሰርተዋል የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል በክርስቶስ በሆነው ቤዛነት በኩል እንዲያው በጸጋው ይጸድቃሉ  ››  ሮሜ.3፤20-23 ይላል፡፡ 'ልዩነት የለም'  የሚለው ቃል ጻድቅ  እንደሌለ እና በራሱ ተቀባይነትን በእግዚአብሔር ፊት ያገኘ አንድም እንደሌለ ነው የሚያሳየው፡፡ ስለሆነም በክርስቶስ በኩል በእምነት የሆነው የእግዚአብሔር ጽድቅ ወደ ሰዎች መጣ  /ሮሜ.5፤1/፡፡

       ‹‹እንግዲህ በአንድ በደል ምክንያት ፍርድ ለኩነኔ ወደ

         ሰው ሁሉ እንደ መጣ እንዲሁም በአንድ ጽድቅ

         ምክንያት ስጦታው ህይወትን ለማጽደቅ  ወደ ሰው

         ሁሉ መጣ፡፡በአንዱ ሰው አለመታዘዝ  ብዙዎች ኀጢያተኞች

         እንደሆኑ እንዲሁ ደግሞ በአንዱ መታዘዝ ብዙዎች

         ጻድቃን ይሆናሉ፡፡›› ሮሜ.5፡18 ና 19

እግዚአብሔር ያዘጋጀው ጽድቅ በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን የሚገኝ ጽድቅ ነው፡፡ እንጂ ህግን በመፈጸም ና በጎ ተግባራትን በመከወን  አይደለም /ሮሜ.3፡28/፡፡ በአዲስ ኪዳን ዘመን ጻድቅ ማለት በጌታችንና በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ  አምኖ የዳነ፣ በደሙም ኀጢያቱን የታጠበ እና በክርስቶስ በኩል ከእግዚአብሔር ጋር ታርቆ በጽድቅ እየኖረ ያለ ሰው ነው፡፡

ክርስቶስ ለተወሰነ ህብረተሰብ ክፍል አይደለም የሞተው ::ለዓለም ሁሉ እንጂ፡፡ስለዚህም ነው መድኀኒዓለም ብለን የምንጠራው፡፡የእርሱ ስቅለትና ሞቱ እኛን ለማዳን በቂ ነው፡፡ለኀጢያታችን የከፈለው ዋጋ፣የፈሰሰው ደም፣የተሰቃየው ስቃይ የሁላችንን እርግማን ለመሻር ና ዕዳችንን ለመክፈል በቂ፣ ከበቂም በላይ ነው፡፡አባቱ በቂ አይደለም! ብሎት በነበረ ኖሮ ሌሎች ተጨማሪ የመዳን ስራዎችን በሰራን ነበር፡፡ነገር ግን እኛን ለማዳን ያነሰ ና የቀረ ነገር አልነበረም የመስቀሉ ስራ አብን አርክቶታል፡፡ ተፈጸመ ብሎኣል፡፡ ስለዚህ ጽድቅ  የማግኛው መንገድ ክርስቶስ ብቻ እንደሆነ ዮሐንስ በወንጌሉ ላይ ምዕራፍ 14 ቁጥር 6  እንዲ ይላል፡-" እኔ መንገድና እውነት ህይወትም ነኝ፡፡በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም፡፡"  'በእኔ በቀር'  የሚለው ከጌታችን ኢየሱስ  በስተቀር ማንም ማዳን እንደማይችል ያሳያል፡፡