Wednesday, January 28, 2015

ሰጥቶም ነስቶም...!

                               ሰጥቶም ነስቶም ሲያየን?!

ብዙ ጊዜ በህይወታችን የምናልፋቸው ሁለት ነገሮች አሉ፡፡አንደኛው ማግኘት ሲሆን ሁለተኛው ማጣት ይሆናል ፡፡ይህ  ምናልባት ገንዘብ ነክ በሆነ ጉዳይ ብቻ ላይሆን ይችላል፡፡አንዳንድ ጊዜ ደስ የሚሉ ቀኖች በህይወታችን ይከሰታሉ፤ ሌላ ጊዜ ደግሞ መኖርንና መፈጠርን እስኪያስጠላ ድረስ ሊኮን ይችላል፡፡ደግነቱ የመከራና የችግር ዘላለማዊ ማህተም ማንም ላይ ስላልታተመ፤ ደግሞ ከደረሰብን ጉዳትና ከገጠሙን ችግሮች በጸጋው አገግመን ሌላ ደስታና ሰላም ውስጥ ስለምንገባ እግዚአብሔር ይመስገን ፡፡

 ለዛሬው ርዕሳችን የኢዮብን ህይወት በመጠኑ ብንዳስስ አሰብኩ፡-ኢዮብ  ትልቅ የሚባል መከራ ውስጥ የነበረ ጻድቅ ሰው ነበር ፡፡ ለምን ያን ሁሉ መከራ ደረሰበት ?  የነበረውን ያን ሁሉ ሐብት እንዴት በአንድ ጊዜ አጣ ?  የሚስቱ መኮብለል፡የልጆቹ መሞት፣የወዳጆቹን ማጣት፣ከዚህ ሁሉ ጋር የእርሱ በቁስል መመታት ...ለኢዮብ ምን ያህል አስከፊ ወቅት እንደነበር መገንዘብ አያዳግትም፡፡ይህ  ሁሉ ለምን እንደ ደረሰበት ኢዮብ በጊዜው የገባው ነገር ባይኖርም ለእኛ ለአንባቢዎች ግን የተገለጠ ነገር አለ፡፡ቃሉ እንደዚህ ይላል፡-

‹‹....እግዚአብሄርም ሰይጣንን  በውኑ  ባሪያዬን ኢዮብን ተመለከትከውን?  እንደሱ ፍጹምና ቅን  እግዚአብሄርን የሚፈራ ከክፋትም የራቀ ሰው የለም ሰይጣንም ለእግዚአብሔር እንዲ ብሎ መለሰለት በውኑ ኢዮብ እግዚአብሔርን የሚፈራ በከንቱ ነውን ? እርሱንና ቤቱን በዙሪያውም ያሉትን ሁሉ አላጠርህለትምን?.... ነገር ግን እጅህን ዘርግተህ ያለውን ሁሉ ዳስስ በእውነት በፊትህ ይሰድብሀል፡፡እግዚአብሔርም ሰይጣንን እነሆ ለእርሱ ያለው ሁሉ በእጅህ ነው ነገር ግን በእርሱ ላይ እጅህን አትዘርጋ አለው፡፡›› ኢዮብ 1፤6-12



ከላይ እንደተገለጸው ሰይጣን የኢዮብን መስግድ፣የሰርክ መስዋዕት ለእግዚአብሔር ማቅረብ ና ማምለኩን፤ ከበዛለት ጥበቃና ከተደረገለት አንጻር ብቻ እንደሆነ ነው  እያስረዳ የነበረው፡፡ ነገሩ እንካ በእንካ አይነት ነው፡፡ እግዚአብሔር ደግሞ የኢዮብ መሰጠትና አምልኮ  ከሁኔታዎች ጋር የተያያዘ አይደለም አለ፡፡በኢዮብ ላይም ከነበረው ጽኑ መተማመን አንጻር ሲሆንለት፣ ሲበዛለት ያመልካል፡፡ ከነጠከው ና ከነሳኸው ግን በፊትህ ይሰድብሀል፡ ተብሎ እየተከሰሰ ያለውን ሰው ሒድና አረጋግጥ፣ ያለውን ሁሉ ጉዳበት፡ እርሱን ግን ተው ብሎ ፈቀደለት፡፡

ጌታ እንዲህ ሊተማመንብን ይችል ይሆን? ብዙ የተደረገላቸው እና አላቸው የሚባሉ ሰዎች ቢነሳቸው በቤቱ ይቀጥላሉ ወይ?  በተቃራኒው ምንም የለሌላቸው ሰዎች ሲሆንላቸውና ሲሳካላቸው  የድሮውን ፍርሀትና አምልኮ ይቀጥላሉ ወይ?  ከችግር፣ ድህነታቸው ከተላቀቁ በሁዋላ  ጸባያቸው የተቀየረ የድሮውን እግዚአብሔርን መፍራታቸውን ትተው፣የሰርክ፤የማለዳ  ጸሎታቸውን ትተው በመዝናናት የተኩ ስንት ናቸው?  የሰጣቸው ነገር ከሰጪው ያራቃቸው ስንት ናቸው?  ከቤተ ክርስቲያን ፣ከተለያዩ መንፈሳዊ ህብረቶች እርቀው ያሉ ስንት ናቸው?

እግዚብሔር ግን ስለ ኢዮብ በድፍረት ተናገረ፡፡ ባይኖረውም ያመልከኛል፡፡የእርሱ ከእኔ ጋር መሆን ነገሮች አይደሉም ምክንያቱ ...እርሱ እኔን እንጂ  ያለኝን ብቻ ፈላጊ አየይደለም!  እንደማለት ነው፡፡

በዚህ ጉዳይ ኢዮብ ተፈትኖ ያለፈ ይመስላል፡፡ ለአብነት ያህል ሚስቱ እግዚአብሔርን ስደብና ሙት ብላ ከተናገረችው በሁዋላ  ኢዮብ ከመለሰው ክፍል እንኩዋ ብናይ ኢዮብን  በቀለላሉ መረዳት ይቻላል፡‹‹..በዚህ ሁሉ ኢዮብ በከንፈሩ አልበደለም፡፡›› ም.2፤9-10 :: ኖሮት በድሎት  ያመለከውን ጌታ አጥቶ ነጥቶም እርሱ ጻድቅ ነው ብሎ መስክሩአል፡፡  እግዚአብሄርም ስለ እርሱ የተናገረው ለሶስቱ ሰዎች "እንደ ባሪያዬ ኢዮብ ስለ እኔ ቅንን ነገር አልተናገራችሁም" ኢዮብ 42፤8--፡፡

ምናልባት በቅዱሳን ህይወት የተለያዩ ፈተናዎች ሊገጥሙ ይችላሉ፡፡ለምሳሌ የሚወዱዋችሁ ሰዎች ቢጠሉዋችሁ፣ በቤተሰብ አካባቢ ያልታሰበ ነገር ቢገጥማችሁ፣ በዙሪያችሁ ያሉ ደስ የሚሉ ነገሮች ድንገት ቢቀየሩ፣ የተማመናችሁበትን ስራ ብትለቁ፣ምናልባት ኑሮ እንደ በፊቱ ባይሆንላችሁ፣ ብርቱ ወዳጆቻችሁ / ያመናችሁት ሰው / ቢከዳችሁ፣ነገሮች እንደምትፈልጉት ሳይሆኑ ሲቀሩ....ወዘተ እንደ ድሮአችሁ አምልኮአችሁን ትቀጥላላችሁ ወይ ? ነው ፈተናው፡፡

ከድህነትና ባለጠግነት ጋር በተያያዘ ጠቢቡ ሰለሞን የተናገረው አንድ ነገር አለ ‹‹ድህነትንና ባለጠግነትን አትስጠኝ ነገር ግን የሚያስፈልገኝን  እንጀራ ስጠኝ: እንዳልጠግብ እንዳልክድህም  እግዚአብሔር ማን ነው? እንዳልል ድሀም እንዳልሆን እንዳልሰርቅም በአምላኬም ስም በሐሰት እንዳልምል. ››  /ምሳ 30፤8-9/  ከቃሉ አንጻር የድሀ ፈተናው ከማጣቱ የተነሳ በእግዚአብሄር ስም ሀሰት እንዳይናገር ሲሆን ፤ የባለጠግነት የጎንዮሽ ችግር ደግሞ: እግዚአብሔር ማን ነው? የማለት፤ ‹ገነንዘብ ካለ በሰማይ መንገድ አለ.› እስካለኝ ድረስ ማንም ምንም ሊያደርገኝ አይችልም!! የሚል አጉል ትዕቢት ውስጥ መግባት ነው፡፡ ስለዚህ ነው ልከኛ የሆነ ኑሮን ለራሱ የተመኘው፡፡ለነገሩ በሁለቱም ጎን /ሳይዶች/  ችግሮቹ እየታዩ ነው፡፡ አንዳንድ የአፍሪካ ድሆች  ለምን አፍሪካዊ ሆንን? ለምን ጠቆርን? ለምን ይሄ ና ይሄ የለንም ?  የሚሉ ጥያቄዎችን አንግበው የክህደት አቅጣጫ ሲይዙ:: ባለጠጋዎቹ ደግሞ ሌሎችን በመናቅ፣ለራሳቸው የተለየ ስፍራን በመስጠት ተነጥለው ይኖራሉ፡፡

       ሰዎች የተለያየ በረከት ሲሰጣቸው እና ስኬት ውስጥ ሲገቡ ሊያስቡዋቸው የሚገቡ ጥቂት ቁም ነገሮች አሉ፡፡ምናልባትም ለክፉ ነገር እንዳንነሳሳ እንደ ማርከሻ ልንጠቀምበት እንችላለን፡፡ ከዚያም  በችግር ወቅት ምን ማሰብ እንዳለብን  ጥቂት እናያለን፡፡

1- ትናንትናን/መነሻችንን/ አለመርሳት

 ‹‹ዛሬ  አንተን የማዘውን ትዕዛዙንና ፍርዱን ስርዓቱን ባለመጠበቅ አምላክህን እግዚአብሔርን እንዳትረሳ ተጠንቀቅ፤ከበላህና ከጠገብክ በሁዋላ ፣መልካምም ቤት ሰርተህ  ከተቀመጥክ በሁዋላ ፣የላምና የበግ መንጋ ከበዛልህ በሁዋላ .፣ ብርህና ወርቅህ ያለህም ከበዛልህ በሁዋላ ፣ልብህ እንዳይጉዋደድ.....አምላክህን እግዚአብሔርን እንዳትረሳ፤ በልብህም ጉልበቴ የእጄም ብርታት ይህን ሀብት አመጣልኝ እንዳትል፡፡›› ዘዳግም 8፤11-18

2- የተሰጠኝ ነገር በጎ ስራ እንድሰራበት ነው በሚል ዕቅዶችን ማውጣትና ሌሎችን በመርዳት ጉዳይ መንቀሳቀስ

 ‹‹ በአሁን ዘመን ባለጠጎች የሆኑት የትዕቢትን ነገር እንዳያስቡ ደስም እንዲለን ሁሉን አትርፎ በሚሰጠን በህያው እግዚአብሔር እንጂ በሚያልፍ ባለጠግነት  ተስፋ እንዳያደርጉ እዘዛቸው ፡፡እውነተኛውን ህይወት ይይዙ ዘንድ ለሚመጣው ዘመን ለራሳቸው መልካም መሰረት የሚሆንላቸውን መዝገብ እየሰበሰቡ መልካምን እንዲያደርጉ በበጎም ስራ ባለጠጎች እንዲሆኑ ሊረዱና ሊያካፍሉም የተዘጋጁ እንዲሆኑ ምከራቸው፡፡  ›› 1ጢሞ.6፤17-19

ብዙዎች በአሁን ጊዜ ከረሀብና ከጥጋብ የትኛው ያስቸግራል ? ብለው ይጠይቃሉ፡፡አንዳንዶች እንደ ዳዊት በችግር /በስደት/  ዘመን ታማኝ ሆነው ኖረው ፤ሲነግሱ ሲያልፍላቸው የሚበድሉ አሉ፡፡ዳዊት ከነገሰ በሁዋላ ነው አስከፊ በደሎችን የሰራው ፤በሰራዊቱ ልቡ የታበየው፤ የታማኝ ወታደሩን የኦርዮንን ሚስት የደፈረው፡፡ሌሎች ደግሞ በችግር ወቅት የጣሉት ብዙ መንፈሳዊ ነገር  አለ፡፡ ለምሳሌ ኤሳው ውድ የሆነ ብኩርናውን ለሚጠፋ መብል የለወጠው በራበው ጊዜ ነው፡፡

3-  በጊዜውም አለጊዜውም መጽናት.........ቃሉ በህይወት የሚገጥሙ ሁለቱን ገጽታዎችን ነው የሚጠቁመን፡፡በጊዜው የሚለው የሚመችና ደስ የሚለውን ቀናት ሲሆን፤ያለ ጊዜው የሚለውz ደግሞ ደስ አይሉም የምንላቸውን የማይመቹ ክፉ ቀናትን ነው፡፡

ምናልባት በዚህ ጊዜ በማይመች ሁኔታ ውስጥ ያላችሁ ይህ ዘመን አልፎ ሌላ የበረከት ሁኔታ ውስጥ ትገባላችሁ ብዬ በጌታ ታምኜ እነግራችሁዋለሁ፤ ነገር ግን ሁሌም የማይለወጥና ያው የሆነ ህይወት እስከመጨረሻ እንድንይዝ  አስቀድመን ልንጸልይ ይገባል፡፡በተደላደለ ሁኔታ ያላችሁም ሰዎች ምንም ማድረግ የማትችሉበት ክፉ ቀን ሲመጣባችሁ ታማኝነታችሁ ሳይጎድል ጌታን መጠበቅ እንድትችሉ ተግቶ መጸለይ ያሻል፡፡

በመጨረሻ ሰጥቶም ነስቶም ቢያየን ያው አምላኩን የሚፈራና የሚያመልክ አውነተኛ ክርስቲያን ሆነን አንዲያገኘን ጌታ በዘላለማዊ ጸጋው ይርዳን በማለት በሮሜ 8 ላይ የተጠቀሰውን ሐሳብ ወስጄ ትምህርቴን አጠቃልላለሁ ፤ጳውሎስ እንደጠቀሰው ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየኛል ? ይልና ሁለቱን ዓይነት ገጽታዎች ያስቀምጣል ፡፡ በተለይ " ከፍታም -ዝቅታም" የሚለው ቃል ውስጤን ይስበዋል፡፡ በህይወታችን በተለያየ መንገድ ከፍታ ሲመጣም ፣ ደግሞ ዝቅታዎች ሲገጥሙን ዘላለማዊው ፍቅሩ ያለመናወጥ ውስጣችን ይደር አሜን፡፡.

አስተያየት ና ጥያቄ ደግሞ የጸሎት ርዕስ ካለዎት በአድራሻው ይጻፉ፡፡  benjabef@gmail.com


No comments:

Post a Comment