Saturday, January 31, 2015

አማላጅነት!

                                      አማላጅነት

                                    /ክፍል- 1 /

ክርስቶስ ፈራጅ ነው /አማላጅ  ?

የጻድቃን አማላጀነት ያስፈልጋል ወይ ?

የመላዕክት ድርሻስ ምንድን ነው ? የሚሉትን ነገሮች በስፋት እንዳስሳለን፡፡

በቅድሚያ ጻድቅ የሚባለው ማን ነው?  ምን ያደረገ ነው?  የሚለውን መሰረታዊ ጥያቄ መጽሀፍ ቅዱስ ላይ ተመስርተን እንመልስ፡ ጻድቅ ማለት በእግዚአብሔር ፊት ትክክል የሆነ ፣ተቀባይነትን ያገኘ ማለት ሲሆን፡፡ ህግጋትን በመፈጸምና አንድም ሀጢያት ባለመፈጸም የታወቀው ብቸኛ ሰው የሆነው ደግሞ ክርስቶስ ብቻ ነው፡፡ ሌሎች ሰዎች ሁሉ በደልን እንደሰሩ ቃሉ እንዲህ ይላል፡ ‹‹ልዩነት የለምና ሰዎች ሁሉ ኃጢያትን ሰርተዋል የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሎአቸዋል በክርስቶስ በሆነው ቤዛነት በኩል እንዲያው በጸጋው ይጸድቃሉ  ››  ሮሜ.3፤20-23 ይላል፡፡ 'ልዩነት የለም'  የሚለው ቃል ጻድቅ  እንደሌለ እና በራሱ ተቀባይነትን በእግዚአብሔር ፊት ያገኘ አንድም እንደሌለ ነው የሚያሳየው፡፡ ስለሆነም በክርስቶስ በኩል በእምነት የሆነው የእግዚአብሔር ጽድቅ ወደ ሰዎች መጣ  /ሮሜ.5፤1/፡፡

       ‹‹እንግዲህ በአንድ በደል ምክንያት ፍርድ ለኩነኔ ወደ

         ሰው ሁሉ እንደ መጣ እንዲሁም በአንድ ጽድቅ

         ምክንያት ስጦታው ህይወትን ለማጽደቅ  ወደ ሰው

         ሁሉ መጣ፡፡በአንዱ ሰው አለመታዘዝ  ብዙዎች ኀጢያተኞች

         እንደሆኑ እንዲሁ ደግሞ በአንዱ መታዘዝ ብዙዎች

         ጻድቃን ይሆናሉ፡፡›› ሮሜ.5፡18 ና 19

እግዚአብሔር ያዘጋጀው ጽድቅ በልጁ በኢየሱስ ክርስቶስ በማመን የሚገኝ ጽድቅ ነው፡፡ እንጂ ህግን በመፈጸም ና በጎ ተግባራትን በመከወን  አይደለም /ሮሜ.3፡28/፡፡ በአዲስ ኪዳን ዘመን ጻድቅ ማለት በጌታችንና በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ  አምኖ የዳነ፣ በደሙም ኀጢያቱን የታጠበ እና በክርስቶስ በኩል ከእግዚአብሔር ጋር ታርቆ በጽድቅ እየኖረ ያለ ሰው ነው፡፡

ክርስቶስ ለተወሰነ ህብረተሰብ ክፍል አይደለም የሞተው ::ለዓለም ሁሉ እንጂ፡፡ስለዚህም ነው መድኀኒዓለም ብለን የምንጠራው፡፡የእርሱ ስቅለትና ሞቱ እኛን ለማዳን በቂ ነው፡፡ለኀጢያታችን የከፈለው ዋጋ፣የፈሰሰው ደም፣የተሰቃየው ስቃይ የሁላችንን እርግማን ለመሻር ና ዕዳችንን ለመክፈል በቂ፣ ከበቂም በላይ ነው፡፡አባቱ በቂ አይደለም! ብሎት በነበረ ኖሮ ሌሎች ተጨማሪ የመዳን ስራዎችን በሰራን ነበር፡፡ነገር ግን እኛን ለማዳን ያነሰ ና የቀረ ነገር አልነበረም የመስቀሉ ስራ አብን አርክቶታል፡፡ ተፈጸመ ብሎኣል፡፡ ስለዚህ ጽድቅ  የማግኛው መንገድ ክርስቶስ ብቻ እንደሆነ ዮሐንስ በወንጌሉ ላይ ምዕራፍ 14 ቁጥር 6  እንዲ ይላል፡-" እኔ መንገድና እውነት ህይወትም ነኝ፡፡በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም፡፡"  'በእኔ በቀር'  የሚለው ከጌታችን ኢየሱስ  በስተቀር ማንም ማዳን እንደማይችል ያሳያል፡፡

አማላጅነት የሚለው ቃልና ሀሳብ ብዙ የተሳሳቱ ትርጉም ሲሰጣቸው ይስተዋላል፡፡ማማለድ ማለት ማስታረቅ፣ማስማማት ማለት ነው:: ይህን ነገር በሁለት ሊስማሙ በሚገባቸው መሀል ገብቶ የሚፈጽመው ሰው አማላጅ /አስታራቂ / ይባላል፡፡ለምሳሌ በዚህ ዘመን እንደሚታወቀው አንድ አገር ከሌላ አገር ጋር ሲጣሉ ሊሸመግሉ የሚገቡት ከተጣሉት አገራት በብዙ ነገራቸው የሚበልጡና ከፍ ያሉ አገራት ናቸው፡፡ለምሳሌ ሁለቱ ሱዳን አገራትን እያስማሙ ያሉት አገራት ፕሬዝዳቶችን ብናይ በፍጹም ከተጣሉት ያነሱ አይደሉም እንደውም ብዙ ጊዜ ከበድ ያለ ሰው ሲመጣ ሽምግልናው ይሳካል፡፡በቤተሰብ ደረጃም ብንሔድ ልጅ ከአባቱ ወይም ከእናቱ ጋር ቢጣላ ወደ ወላጆቹ ለዕረቅ የሚላከው ሰው እናትና አባት ሊሰሙትና ሊያከብሩት የሚችሉት ሰው መሆን አለበት፡፡ይህን ሁሉ የምንለው ማማለድ ማለት የማነስ ምልክት አይደለም ለማለት ነው፡፡

ታዲያ ሰውና እግዚአብሄርንም ለማስታረቅ ከሰውም ሰው የሆነ: ከእግዚአብሔር ጋርም እኩያ የሆነ አስፈላጊ ነበር፡፡ ክርስቶስ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር እኩል የሆነ አምላክ በመሆኑ የማማለድን ስራ ሰራ፡፡ እርቁ ግን ከአብ ጋር ብቻ ሳይሆን ከራሱም ጋር ነበር፡፡

ይማልዳል / ያስታርቃል/ ሲባል ተንበርክኮ ይለምናል ፣ዝቅ ብሎ ይለማመጣል ማለት አይደለም፡፡እንኩዋን እርሱ ከላይ የጠቀስናቸው የአገራት ሽማግሌዎች  ተደፍተው አይለምኑም፡፡ነገር ግን ለሰው ልጆች ሁሉ ቤዛ የሆነበት ደሙ በአብ ፊት ዘውትር ይታያል ማለት እንጂ፡፡ስለዚህም ነው የዕብራውያን ጸሐፊ ሲጠቅስ ''እርሱ ግን ስለ ኀጢያት አንድን መስዋዕት ለዘላለም አቅርቦ በእግዚአብሔር ቀኝ  ተቀመጠ፡'' የሚለን፡፡ ዕብ. 10፤12  በተጨማሪ  9፤28ን ያንብቡ፡፡

አሁን በሰማይ እገሌንም ይቅር በለው እገሊትንም ይቅር በላት እያለ የሚለመንበት ዓይነት የምልጃ ስርዐት  ይኖራል ብለን አንጠብቅም፡፡ በክርስቶስ በኩል የቀረቡትን ሁሉ  ከሐጢያትና ከበደል ነጻ የሚያደርግ ቅዱስ  ደም ግን አለ፡፡ ደሙ ስለ ሁላችን ሐጢያት ማስተሰርያ እንዲሆን የፈሰሰ ነው፡፡

ክርስቶስ ስለ እኛ ይማልዳል! የሚለውም ቃል /ሮሜ 8፤34/ ከላይ በተገለጠው አግባብ ካልተፈታ በቀር ሌላ ነገር እንድንረዳ ሊያደርገን ይችላል፡፡አምላክ ሆኖ እንዴት ዝቅ ይላል እንዴት ይማልዳል ? ክርስቶስ ፈራጅ ነው አማላጅ?  የሚሉ ጥያቄዎች/ አሳቦች/ በስፋት  ይነሳሉ ፡፡ለነገሩ አምላክ ሆኖ እንዴት ያማልዳል? ከሚለው ነገር ይልቅ አምላክ ሆኖ እንዴት ይሞታል? የሚለው ነው ከባድ መሆን የነበረበት፡፡ነገር ግን አምላክ የሆነው ኢየሱስ  መከራን ተቀብሎአል፣ ተገርፎአል፣ ተሰቅሎአል፣ ሞቶኣል፡፡የማዳን ስራውም ተፈጽሞአል፡፡ ወደ እርሱ የሚቀርቡ ማናቸውም ሰዎች በደሙ ነጽተው ይጸድቃሉ፡፡እርሱ በስጋው ወራት የከፈለው የሀጢያት ክፍያና ከብርቱ ጩኸት ጋር ያቀረበው ምልጃ፣ አጠቃላይ የመስቀል ስራው ህያው ሆኖ ወደ እርሱ ለሚቀርቡት ሁሉ ይታይላቸዋል፡፡ክፍያው ስለ ሰው ልጅ ሁሉ  ነውና፡፡

የጻድቃን ምልጃ

ጻድቃን በምድር ሳሉ በምድር ላይ ገና በህይወት ላሉት ሰዎች ሊጸልዩ ና ሊያማልዱ ይችላሉ፡፡ የጌታችን የኢየሱስ እናት ቅድስት ማርያምም አማልዳለች፡፡የሰዎችን ጉዳይ ለልጁዋ ነግራለች ከዚህም በላይ ከበጉ ሐዋርያት ጋር አብራ ጸልያለች፡፡ምናልባት ወንጌል ገና ስላልደረሰበት የአለም ክፍሎች አሳስበው ይሆን?  ሌላም ብዙ የሰዎችን የተወሳሰበ ጉዳየ ይዘው በእግዚአብሔር ፊት በጸሎት ቀርበው ይሆናል፡፡ምን እንደ ጸለዩ ነው እንጂ የማናውቀው መጸለያቸውን እናውቃለን፡፡ሐዋ. ስራ 1፤14፡፡

አለምን ሁሉ ከአብ ጋር የማስታረቅና የማዳን ስራ ግን የተሰራው በጌታችንና በመድሐኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የመስቀል ስራ በመሆኑ፤ ጻድቃንም ሆኑ ሰማዕታት ሰዎችን የማዳንም ሆነ መንግስተ ሰማይ የማስገባት ስልጣን አልተሰጣቸውም፡፡ የዘላለም ህይወት ጉዳይ እንዲህ ቀላል ነገር ቢሆንማ ኖሮ  ክርስቶስ መጥቶ ባልተሰቀለ፤ያን ሁሉ ዋጋ ባልከፈለ ነበር፡፡ እርሱ በስጋ ሳይወለድ እኮ ነብያት፣ አባቶች፣ ነበሩ፡፡ግን መዳን በእነርሱ በኩል ሊፈጸም የሚችል ጉዳይ ባለመሆኑ ነው የጌታችን መምጣት የግድ የሆነው፡፡

ከመዳን ጉዳይ ባሻገር ለተለያዩ ጉዳዮችም ቢሆን የሞቱ ቅዱሳን በህይወት ስላሉት ሊለምኑና የሰዎችን ጸሎት ሁሉ ሊሰሙ  እንዴት ይችላሉ? በመጀመሪያ ከፈጣሪ በስተቀር ሁሉ ፍጡራን  ናቸው፡፡ምድራዊ እናትና አባት ኖሮአቸው የተወለዱ በጊዜና በስፍራ የተወሰኑ ናቸው፡፡ ስለዚህም ነው መሞታቸው፡፡ ከላይ ሆነው ሁሉን ማየት እንደ እግዚአብሔር ከቻሉ እኮ: መለኮት ሆነዋል ማለት ነው ፤ግን እንደዛ አይደለም፡፡

              መላዕክት

በዚሀም ላይ መላዕክት እንኩዋ ቢሆኑ እልፍ አዕላፋት የሆኑት፤ አንድ መልዐክ ሁሉ ቦታ በአንድ ጊዜ መገኘት ስለማይችልና ሁሉንም በአንድ ጊዜ መስማት ስለማይችል ነው፡፡ለምሳሌ አብሳሪውን የጌታ ታማኝ መልዐክ ቅዱስ ገብርኤልን እንውሰድ ዕለተ ቀኑ በሚባለው 19 ምናልባት ታህሳስ 19  ንግስ ተብሎ በሚነገረው ቀን ፤ካሉት በርካታ በስሙ የተሰየሙ አብያተክርስቲያናት መካከል መርጦ የሚገኘው የትኛው ክልል ነው? የትኛውስ ቤተክርስቲያን ነው? ምክንያቱም አንድ ነው ብለናል፡፡ ሁሉን መቻል / Omnipotent /፣ ሁሉን ማወቅ / Omniscience  /፣ በአንድ ጊዜ በሁሉም ስፍራ መገኘት / Omnipresent    / የእግዚአብሔር ብቻ የሆነ ባህሪ ነው፡፡ሁሉም ጻድቃን፤ መላዕክት ሁሉን ማወቅ፤በሁሉ ቦታ በአንድ ጊዜ መገኘትና የሁሉን ሰው ጸሎት ማድመጥ የሚችሉ ከሆነ እግዚአብሔር የሚባለው አምላክ ምን ልዩነት አለው ታዲያ?  ነገር ግን እውነቱ እነዚህ ባህርያት ማንንም ያላጋራበት የስላሴ ብቻ የሆነ ነው፡፡ ስላሴን የተለየ የሚያደርጋቸውም ይህ ባህሪ ነው፡፡

ለምሳሌ ቅዱስ ገብርኤል የኢየሱስን እናት ማርያምን ሊያበስራት የመጣ ጊዜ እርሱን ሌላ ቦታ ማግኘት አይቻልም፡፡ ምናልባት በዚያ ጊዜ አጣዳፊ ጉዳይ ካለ እንኩዋ ሌላ መልአክ ነው የሚላከው:: ምክንያቱም አንድ መልዐክ መገኘት የሚችለው በአንድ ቦታ ብቻ ስለሆነ ነው፡፡ ከዚህ ሌላ ወደ ዳንኤል መልስ ይዞ  እየበረረ ይመጣ የነበረውን መልዐክ  /አንዳንድ ሰዎች ገብርኤል  እንደሆነ ይላሉ/  የፋርስ አለቃ  (የፋርስ መንግስት አገር  ላይ በአየሩ ላይ አለቃ የነበረ አጋንንት) እንዳያልፍ ከልክሎት እንደነበር፤ ለ 21 ቀናትም ተቸግሮ እንደነበር ማወቁ ጥሩ ነው፡፡በሁዋላም ወደ ዳንኤል መምጣት የቻለው የመላዕከት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል ሊረዳው ስለመጣ ነበር /ዳን.10፤13-20/፡፡ መላዕክት ሲላኩ በቦታ በስፍራ የሚወሰኑ መሆናቸውን ተመለከታችሁ? እንዳይመጣ ተከልክሎስ እንደ ነበረ አያችሁ?

መላዕክቶችም ሆኑ ቅዱሳን ወደ ጠሩአቸው ሁሉ የመሄድ፣ እንደወደዱ የማድረግ ማንነት አይደለም ያላቸው፡፡ መላዕክትነታቸው ለእግዚአብሔር ነውና እርሱ ወደ ላካቸው ሁሉ ይሄዳሉ፡፡ እርሱ ያዘዛቸውንም ይፈጽማሉ፡፡ ይህን እውነት ማወቅና መናገር እነርሱን ማዋረድ ማለት አይደለም፡፡ በፍጹም እነርሱን ዝቅ ማድረግም አይደለም፡፡ እውነት አርነት ያወጣል፡፡አብርሐም ቤት የመጡት መላዕክት አብርሀም ቤት ጉዳያቸውን ሲፈጽሙ ነው  ሎጥ ዘንድ ሰዶም የሄዱት፡፡

ከመጀመሪያው ግን ከዘላለም  ሞት እንዲያድኑንና እንዲያስታርቁን ተሹመው በነበረ ፡አለመታዘዛችን ነበር ሀጢያት የሚሆን፡፡እነርሱም ብዙ በታዘቡን ነበር፡፡ አሁን ግን ከገረማቸው እንኩዋ  ሊገርማቸው  የሚችለው እነርሱ  ለእረኞች ያበሰሩትን ጉዳይ ያለመታዘዛችንን ሲያዩ ነው  /ሉቃ.2፤9-14/፡፡ የፃድቃንም አግራሞት ለእነርሱም መደሀኒት ወደ ሆነው ወደ ክርስቶስ አለማተኮራችን ነው፡፡ ቅድስት  ማርያምም ከገረማት እንኩዋ የሚገርማት ‹አርሱን ሰሙት›  ያለችውን፣ መድሀኒቴ አምላኬ ባለችው ልጁዋ አለማመናችን ነው፡፡ስለ ሁሉም ክርስቶስ ከመምጣቱ በፊት በመስቀል ላይ ስለ ከፈልክልኝ ዋጋ አመሰግንሀለሁ፡፡በቀራንዮ መስቀል በፈሰሰው ደምህ ሀጢያቴን እጠብልኝ ከበደሌም አንጻኝ፤ወደ ልቤም ገብተህ አብረኸኝ ኑር በማለት ከልባችን  ንስሀ  እየገባን በመጸለይ   ራሳችንን ለመንግስተ ሰማይ እናዘጋጅ፡፡የጌታችን ዳግም ምፅዐት ቀን ተቃርቡዋል፡፡ ከእግዚአብሔር በኩል ያለው ነገር ሁሉ ተሰርቶ አልቁዋል፤ ከእኛ በኩል የቀረውን እናድርግ!! ሰምተን እንድንታዘዝ እግዚአብሔር ይርዳን፡፡አሜን፡፡

አስተያየት ወይም ጥያቄ ካላችሁ ከስር አስተያየት መስጫ ሣጥኑን  / COMMENT   / ተጭነው ይጻፉ፡፡




1 comment:

  1. እግዚአብሔር ይባርክህ ብዙ ተምረበታለሁ ..ስለ ክርስቶስ መካከለኝነት ብቻ ጠለቅ ያለ ማብራርያ ብትሰጠን ደስ ይለኛ ጌታ ኢየሱስ ይባርክህ

    ReplyDelete