Friday, January 23, 2015

ራሱን ካላዳነ...!

               ለዛሬ ደግሞ የህይወትን ሌላ አቅጣጫ የምናይበት ግጥም ቀርቦአል፤  ታስታውሱ እንደሆነ ጌታችን በተሰቀለበት ጊዜ ከጎንና ጎኑ አብረው የተሰቀሉ ወንበዴዎች ነበሩ፡፡ አንደኛው እንደዚህ ብሎት ነበር ፡-" አንተስ ክርስቶስ አይደለህምን ? ራስህንም  እኛንም አድን ብሎ ሰደበው !"/ ሉቃ.23፤39/ ይህ  ሰው ያሰበው ራሱን ካዳነ ለእኛም አያቅተውም የሚል ዓይነት ነው፡፡ ግን መለኮታዊው መርህ  ምን ነበር ? ግጥሙን  ደጋግማችሁ በማንበብ ትምህርት እንደምታገኙበት አልጠራጠርም፡፡ጌታ በነገር ሁሉ ማስተዋልን ይስጠን፡፡በተለይም በመሸነፍ ውስጥ ማሸነፍ እንዳለ ላልተመለከታችሁ የመለኮትን አሰራር እና አደራረግ ትረዱበታላችሁ ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡እሰቲ መሸነፍና ሞኝነት በሚመስል መንገድ ውስጥ እግዚአብሔር የሚሰጠንን ድል እንለማመድ!!



                                ራሱን ካላዳነ !

                   የመከራዋ ቀን ዘግናኝቱ ሌሊት

                   ልብን ከሚሰነቅሩ ብዙ ቃላት

                   በተለይ በተለይ ራስህን አድን የሚለው

                   ራሱን ካዳነ ይሆን የሚያድነው?

                    በራሱ ሲያሳይ ነው በሰው ሚታመነው?

                    እንዲህ ይሆን ወጉ ያገር ፍልስፍናው?

                    ለራሱ ካልሆነ ለእኛ በምኑ ነው!

                    ግን እኮ ራሱን ካዳነ በዚህች ዕለት

                    መከራ ካልነካው ጂራፍ ካልገረፈው

                    ውሀ  ጥም ካልጠማው ደም ላብ  ካላላበው

                    ሰራዊቶች  መጥተው ከሰማይ ከረዱት

                    ደመኞቹን  መጥተው ከተበቀሉለት

                    ወታደር  ከወታደር ጋር ተጋጭቶ

                    ከሰማይ የመጣው የምድሩን ረትቶ

                    ያለ እስራት ፣ያለ ችንካር ፣ያለ ውርደት

                    በሰው አጠባበቅ እንዲ ነው ጀግንነት::

                    ራሱን ካዳነ ለእኛ ምን ሊያቅተው?

                    ለእኛም ያደርገዋል ለእሱ  እንዳደረገው::

                    ነገር ግን እውነቱ  ያንድዬ ብልሀቱ

                     ድነትን ሲቀምር በአዋቂነቱ

                     ካላዳነ ራሱን መድሐኒት ተገኘ

                     በራሱ ሳያሳይ በእኛ ዝናው ናኘ::

                      እርሱ ተገረፈ እኛ ተፈወስን

                      እርሱ ተሰቃየ እኛ ድል አገኘን::

                      ራሱን ካላዳነ ነበር የሚያድነው

                     መለኮት እንደዚህ ድነትን ቀመረው፡፡

                                                                                                    benjabef@gmail.com

No comments:

Post a Comment