Monday, May 4, 2015

ስንት አይነት መፅሐፍ ቅዱስ አለ?

         ክፍል አንድ

መፅሐፍ ቅዱስን በተመለከተ የሚቀርቡ ብዙ የሰዎች አስተያየቶች በመኖራቸው ይህንን ትምህርት ሰፋ አድርጎ ማቅረቡ ተገቢ ሆኖ ተገኝቶአል፡፡ በዚህ ክፍለ ትምህርት ውስጥ በተለይ ጎላ ብለው የሚታዩትን ልዩነቶች እንጂ ተያይዘው የሚነሱትን ሐሳቦችና ጥያቄዎች ሁሉ አንስቶ መፃፍ እንደማይቻል አንባቢ ሊረዳው ይችላል ፡፡ ምክንያቱም እጅግ ሰፊ በመሆኑ ነው፡፡

ከምናነሳቸው ጥያቄዎች ውስጥ ትክክለኛው የመጽሐፍ ቅዱስ  ቁጥር  ስንት  ነው ? የሚለውን ይሆናል፡፡ ምክንያቱም በኦርቶዶክስ 84 ወይም በተለምዶ 81 ፣ ካቶሊክ 72 መፅሐፍትን ስትቀበል ፕሮቴስታንት /ወንጌላውያን አማኞች/ ደግሞ 66 ቁጥር  ያለው መፅሐፍን ይቀበላሉ፡፡ ማናቸው ናቸው ትክክል? ወይም እውነቱን እንዴት ልናገኝ እንችላለን? ብለን መጠየቃችን አይቀርምና፡፡

መፅሐፍ  ቅዱስ የእግዚአብሔር  ቃል ነው፡፡ ይህ ማለት ሰዎች በእግዚአብሔር መንፈስ ተነድተው ፣ በሰዎች ቁዋንቁዋ ና ባህል የተጻፈ እስትንፋሰ እግዚአብሔር ያለበት መጽሐፍ ነው፡፡ /2ጢሞ. 3፡15 ና 1ጴጥ.2፡1/

መጽሐፍ ቅዱስ ሁለት ትልልቅ ኪዳኖች ያሉት ሲሆን በብሉይ ኪዳን  /አሮጌው/ እና አዲስ ኪዳን በመባል ይታወቃሉ፡፡ ብሉዩ በዕብራይስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ የተጻፈ ሲሆን ፤አዲስ ኪዳን ግን በዘመኑ  ታዋቂ በነበረው የግሪክ ቁዋንቁዋ ነበር የተፃፈው፡፡ ከዚያ በሁዋላ  በብዙ መቶ ቁዋንቁዋዎች በዓለም ዙሪያ ተተርጉሞአል ፡፡ በዓለም ላይ አንደኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠ መጽሐፍ ነው፡፡

ከላይ ያነሳነውን  ጥያቄ ለመመለስ የግድ የመጀመሪያዎቹን ትርጉሞችና ቅጂዎች ማንሳት ተገቢ ስለሆነ ነው፡፡ እንደሚታወቀው የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪክ የተፈጸመው በአብዛኛው በዕብራውያን /እስራኤላውያን ህዝብ /መካከል ነው ፡፡ የታሪኮቹ ባለቤቶችና ጸሐፊዎች እዚያ የነበሩ ሰዎች ናቸው፡፡በነገራችን ላይ ቢያንስ አርባ የሚሆኑ ሰዎች እንደጻፉት ይታመናል፡፡ ባለታሪኮቹ እነርሱ ከሆኑ ደግሞ በአሁን ጊዜ ጭምር እጃቸው ላይ ያለና የሚጠቀሙበት መጽሐፍ ምን እንደሚመስል ማወቁ ተገቢ ነው፡፡ ይህም በተለይ ብሉይ ኪዳንን በተመለከተ እንጂ አዲስ ኪዳንን ጉዳይ ላይ አይሆንም ፡፡ ምክንያቱም እስራኤል ስለ ሐጢያታችን በምድራቸው ላይ ሞቶ የተነሳውን መሲሁ ክርስቶስን እስካሁን ድረስ ስላልተቀበሉትና ሌላ መሲህ እየጠበቁ ከመሆናቸው አንጻር ነው፡፡/ሮሜ.9/

የዕብራይስጡ መፅሐፍ ዝርዝር እንደሚከተለው ነው፡-
          /የመጽሐፉ ይዘት 24 ነው፡፡/

1-የሕግ መፃሕፍት /5/
   /አሪት ዘፍጥረት፣ ዘጸዐት፣ ዘሌዋውያን፣ ዘኁልቁ፣ ዘዳግም/

2-የነብያት መጻሕፍት-/8/
  ሀ-ኢያሱ፣ መሳፍንት፣ 1-2 ሳሙኤል፣ 1-2 ነገስት፣
  ለ-ኢሳያስ፣ ኤርሜያስ፣ ሕዝቅኤል፣ 12ቱ የነብያት     መጻሕፍት

3-የጥበብና ምሳሌ መጻሕፍት./ 11/
   ሀ-የጥበብ  መዝሙር ፣ምሳሌ፣ ኢዮብ
   ለ-5ቱ ጥቅል መጻሕፍት . መኃልየ ፣ሩት፣ ሰቆቃው ኤርሜያስ፣ መክብብ፣ አስቴር፡፡
   ሐ-3ቱ መጻህፍት. ዳንኤል፣ ዕዝራ-ነህምያ፣ ዜና መዋዕል

የፕሮቴስታንት ቀኖና እንደሚከተለው ነው፡፡
      / የመጽሐፉ ይዘት 39 ነው፡፡/ 

1- የሕግ መጻሕፍት ./5/
  / ዘፍጥረት፣ ዘጸዐት፣ ዘሌዋውያን፣ ዘኁልቁ፣ ዘዳግም/
2-ታሪካዊ መጻሕፍት./12/
 / ኢያሱ፣ መሳፍንት፣ ሩት፣ 1ሳሙኤል፣ 2 ሳሙኤል፣ 1ነገስት፣ 2 ነገስት፣ 1ዜና መዋዕል፣ 2ዜና መዋዕል፣ ዕዝራ፣ ነህምያ፣ አስቴር፡፡
3-የጥበብ መጻሕፍት./5/
  /ኢዮብ፣ መዝሙር፣ ምሳሌ፣ መክብብ፣ መኀልዬ ዘሰሎሞን/
4- ትልልቅ /አበይት/ ነብያት./5/
  / ኢሳያስ፣ ኤርሜያስ፣ ሰቆቃው ኤርሜያስ፣ ሕዝቅኤል፣ ዳንኤል/
5- ትናንሽ ነብያት. /12/
  / ሆሴዕ፣ ኢዩኤል፣ አሞጽ፣ አብዲዩ፣ ዮናስ፣ ሚክያስ፣ ናሆም፣ ዕንባቆም፣ ሶፎንያስ፣ ሐጌ፣ ዘካርያስ፣ ሚልክያስ/

     ከላይ እንደተመለከተው መጻሕፍቱ በአከፋፈል ረገድ ካልሆነ በቀር በዕብራይስጡ እና በፕሮቴስታንቱ ቀኖና መካከል የይዘት ልዩነት የለውም፡፡/ በኦርቶዶክስና በካቶሊካውያን መካከል እነዚህን መጽሐፍት በተመለከተ ምንም ጥያቄ የሌለ እና ሙሉ ለሙሉ ተቀባይነት ያገኙ መጻሕፍት በመሆናቸው ልዩነቶቹ ላይ ማለትም የተጨመሩ አዋልድ መጻሕፍቱ ላይ ማተኮሩን መርጫለሁ፡፡
 አስቀድመን ከላይ እንዳነሳነው ካቶሊክ የባሮክ፣ ጦቢት፣ ዮዲት፣ ሲራክ፣ 1-2 መቃብያን  ከሚባሉ ጋር 72 መጻሕፍትን፡፡ ኦርቶዶክስ  ደግሞ  ተረፈ ዳንኤል፣ መቃብያን ቀዳማዊ፣ መቃብያን ካልዕ፣ 3ኛ መቃቢያን፣ ሲራክ፣ ጸሎተ ምናሴ፣ ተረፈ ኤርምያስ ፣ ሶስና፣ ባሮክ፣ መጽሐፈ ጥበብ፣ በዕዝራ ሱትኤል፣ ዕዝራ ካልዕ፣ ጦቢት፣ ዮዲት፣ አስቴር፣መዝሙረ ሰልስቱ  ደቂቅ፣ ተረፈ ዳንኤል፣ ኩፋሌ፣ ሄኖክ  የሚባሉ  84 ይዘት ያላቸው መጻህፍት አሉዋቸው፡፡ይህ ማለት ዕብራይስጡ 24 ወይም የ ፕሮቴስታንቱ 39 የሚባሉ የብሉይ ኪዳን ቀኖና መጻሕፍትን ጨምሮ ነው፡፡

አንባቢ እንደሚያስተውለው ዋናዎቹ  የመጻሕፍቱና የታሪክ ባለቤቶች ዕብራውያን እነዚህን አዋልድ ያካተተ መጻሕፍት የላቸውም፡፡ ይህ ማለት የታሪክ ባለቤቶቹ ያልተቀበሉዋቸው መጻህፍት እንደሆነ ልብ ይሉዋል፡፡

ከዚህ በመቀጠል የምንመለከተው የጥንት አባቶቻችን በምን መስፈርት ቀኖናውን /የመጻሕፍቶቹን ይዘትና ዝርዝር / እንደወሰኑ ነው፡፡

     ቀኖና የተወሰነበት  አራት ዋና ዋና መመዘኛዎች ፡-

1- በዋናው የዕብራይስጡ ዝርዝር ላይ የተካተተ መሆኑን፡፡ አስቀድመን እንደተመለከትነው ዕብራይስጡ የራሳቸው የባለታሪኮቹ መጻሕፍ በመሆኑ ከምንም ነገር ይልቅ ቅድሚያ ይሰጠዋል፡፡የዕብራይስጡ መጽሐፍ 24 መጻሕፍትን የያዘ ነው፡፡

2- በአዲስ ኪዳን ዘመን ጌታችን መድሃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምድር ላይ ዘመኑ ዕውቅና ሰጥቶ የጠቀሰው መሆኑ፡፡ ይህም ጌታችን በስጋው ወራት ባስተማረበት ጊዜ ከሙሴ መጽሐፍት፣ ከነብያትና ከመዝሙራት የተነገሩትን ቃላት ይጠቅስ ነበር፡፡በአንድ በኩል መጽሐፍቱ ልብ ወለድ ታሪኮች ሳይሆኑ የእግዚአብሔር ቃል እንደነበሩ ማረጋገጫ ይሰጣል፡፤

3- በሶስተኛ ደረጃ የተቀመጠው የመጀመሪያዎቹ ሐዋርያት ስልጣን ያለው የእግዚአብሔር ቃል እንደሆነ በመጥቀሳቸው ነው፡፡ ይህም ከጌታ በመቀጠል እርሱ ያስተማራቸውና የመረጣቸው አገልጋዮቹ ለብሉይ ኪዳን መፃህፍት ይሰጡ የነበረውን ክብርና ጥንቃቄ፤ ብሎም ጥላውን እያሳዩ ፍጻሜው እንዴት እንደሆነ በመንፈስ እየመረመሩ ይገልጡ እና ይተነትኑ ስለነበረ ሌላው ማረጋገጫ ነበር፡፤

4- የጥንቱዋ ቤተክርስቲያን /ቅዱሳን/ ይህነንን መጽሐፍ እንደ እግዚአብሔር ቃል ይጠቀሙበት እንደነበረ ከታወቀ ቀኖና /canon / ይጸድቅ ነበር፡

ከላይ የተመለከቱትንና ሌሎች እውነታዎችን በማገናዘብ የጥንት አባቶቻችን ቀኖናውን ወስነውልናል፡፡ ከእነዚህ መጻሕፍት ውጪ ያሉት አዋልድ መጻሕፍት የጨለማ ዘመን ተብሎ በሚታወቀው የ 430 የዝምታ ዓመታት ውስጥ አብዛኛዎቹ እንደተጻፉ በስፋት ይታመናል፡፡ ይህም ደግሞ የብሉይ ኪዳን ቀኖና ተወስኖ ከተዘጋ በሁዋላ  የተጨመሩ እንደሆነ የሚጠቅሱ አሉ፡፡ በዚህም ሆነ በዚያ ከተወሰኑ አብያተክርስቲያናት ውጪ መላው ዓለም የሚጠቀምበትን የታወቀውን መጽሐፍ በማንበብ እንድንጠቀም እመክራለሁ፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ቃል መጨመርም ሆነ መቀነስ መርገምን ያስከትላል፡/ራዕይ 22// ‹ ስለ ራዕዩ መጽሐፍ ሲናገር የጨመረ መቅሰፍት ይጨመርበታል ፤ሲል የቀነሰ ደግሞ ዕድሉን ያጎድልበታል፡፡› ይላል፡፡ስለዚህ  መንፈስ ቅዱስ የቤተክርስቲያን አበውን ተጠቅሞ የወሰነልን ፣ለዚህ ህይወታችን ተመጥኖ የተሰጠን ቃል በቂ ነው፡፡እርሱን በቅጡ ለማወቅ ቅን ልቦናችን ቢነሳሳ፣ለማንበብ፣ ለማጥናትና ለማሰላሰል ጊዜ ቢኖረን ህይወት ለዋጭ ቃል ነው፡፤ተግሳጽንም ፣ ታላቅ ምክርን ከጽድቅ ጋር የምንቀስምበት ጭምር፡፡ከዚህ በተጉዋዳኝ ግን በአንዳንድ ወገኖች ዘንድ እንደሚታመነው ተጨማሪ መጻህፍትን ለተጨማሪ እውቀቶች ብናነብ ምንም አይጎዳም! ስለሚሉ፤እንደ ፕሪስቢቴሪያንና አንግሊካል የመሳሰሉ አብያተክርስቲያናት ለዚህ ነገር ዋና ተጠቃሾች ናቸው፡፡ ለዕውቀትም ቢሆን ልንጠቀምበት የምንችለው፡ እውነትን እስካላፋለሰ እና ትክክለኛውን መለኮታዊ የድነትና የህይወት መርህ እስካልበረዘ ድረስ ብቻ ነው ፡፡

             አዋልዱ በቀኖናው ላይ ለምን አልተካተቱም ?

1-   በዕብራይስጡ ዝርዝር ላይ የሌሉና ቀኖናው ከተዘጋ በሁዋላ የተጨመሩ በመሆናቸው ነው፤
2-   በአዲስ ኪዳን ዘመን ያልተጠቀሱ ሲሆኑ፤ አሉ የሚባሉም ካሉ እንደ አባባል የተጠቀሱ እንጂ እንደ እግዚአብሔር ቃል የሚወሰዱ አይደሉም፡፡
3-   የአይሁዳውያን ታሪክ አጥኚ ጆሴፈስ ፈጽሞ አላካተታቸውም፡፡ ይህ ማለት ታሪክ አያውቃቸውም እንደማለት ነው፡፡
4-   አዋልድ  መለኮታዊ ቃል እንደሆነ የሚገልጽ አንድም ማስረጃ የለም፤

5-   የታሪክ፣ መልክዐ-ምድር አቀማመጥ፣ ወይም ጊዜንና ክስተቶችን አዛብቶ የማቅረብ የጎላ ችግር ይታይበታል፡፡ ይህንን በተመለከተ ወደ መጨረሻ ላይ ከአዋልዱ ላይ አንዳንድ ጥቀቅሶችን ስንመለከት የበለጠ ይገባናል፡፡
6-   የእግዚአብሔርን ቃል የሚጻረር ትምህርት /ዶክትሪን/ ያስተላልፋሉ፤ ለምሳሌ፡-ውሸትን ይፈቅዳል፤ ሰይጣንን ያሞጋግሳል....ወዘተ፡
 7-   በስነ ጽሁፋዊ ይዘቱ በታሪክና ምሳሌ ወይም ተረት ውስጥ የሚመደብ ነው፤
8-   መንፈሳዊና ሞራላዊ ይዘቱ / አቁዋሙ/ ከብሉይ ኪዳን አጠቃላይ ታሪክ አንጻር በጣም የራቀ ወይም የወረደ ነው ተብሎ ይታመናል፡፡

     አዋልድ መጻሕፍት  አዛብተው ከሚናገሩት ነገር በጥቂቱ፡-
  • ኩፋሌ 16፤24 ያዕቆብ  ከአብርሐም ጋር ተኛ  ይላል፡፡ ነገር ግን ዘፍ.25፤7 ላይ እንደዚያ አይገልጽም፡
  •  መቃብያን ሳልስ 2፤7 ላይ የሰይጣንን ፉከራ  ይገልጻል፡፡ እንደውም ቃሉ ከቁራን ላይ ቀጥታ የተወሰደ እንደሆነ ያሳያል፡፡ በተጨማሪ 3ኛ መቃብያን 1፡6-24 ፣ ም.2፤1-2 ከቁራን ላይ ከአል አእራፍ ቁጥር 11-27 ከ7ኛው ሱራ ላይ እንደተወሰደ ማመሳከር ይቻላል፡፡
  • መጽሐፈ ጥበብ  6፤6 ላይ ደግሞ በቀጥታ የመዳንን እውነት የሚያፋልስ ሆኖ ቀርቦአል፡
  • ሲራክ 25፤25 እግዚአብሔር በመሰረተው የተቀደሰ ጋብቻ መካከል ሊኖር የማይገባውን ነገር ይናገራል፡፡
  •  ሲራክ 24፤10-11 በተለይም ቁ.8 ላይ ስለ ማርያም፣ ሐዋርያት ና ወንጌል ጉዳይ በግልጽ ያወራል ፡፡ መጽሐፉ በብሉይ ኪዳን ዘመን የተጻፈ አይመስልም፡
  •  እዝራ ሱትኤል 5፤29 ላይ እንዲሁ ስለ መንግስተ ሰማይ ና ስለ ክርስቶስ ይናገራል፡፡ መንግስተ ሰማይ በብሉይ ኪዳን ዘመን በግልጽ ይታወቃልን ?
  •  ሄኖክ 37፤24 ሐጢያተኞች እንድናለን ብለው ተስፋ እንዳያደርጉ ተስፋ ያስቆርጣቸዋል፡፡
  •  ሔኖክ 19፤1 ላይ ቅዱስ ሚካኤል የመንፈስ ቅዱስ እውቀቱ ያበሳጨኛል ብሎ እንደተነናገረ ተገልጹዋል፡፡ በውኑ ቅዱስ ሚካኤል በመንፈስ ቅዱስ እውቀት ይበሳጨጫልን? ሌላም ሌላም በርካታ የተፋለሱ ነገሮችን የያዘ መጽሐፍ እንደሆነ ማየት ይቻላል፡፡ አንባቢያን ተጨማሪ ጥቅሶችን ሲፈልጉ በአድራሻችን ሊጽፉልንና ተጨማሪ እውነቶችን ሊረዱ ይችላሉ፡፡ ለዚህ ጽሑፍ ግን የተጠቀሱት ነገሮች ለማመሳከሪያነት በቂ ሊሆኑ ይችላሉ፡፡

 ማስታወሻ፡- ይህ ትምህርት ከተለያየ መንፈሳዊ መጻሕፍት እና የተዘጋጁ የስልጠና ትምህርቶች  ላይ ተገናዝቦ የቀረበ ነው፡፡

        ለተጨማሪ ትምህርቶች እዚህ ይጫኑ  http://tehadesothought.blogspot.com                       

No comments:

Post a Comment