Tuesday, November 27, 2018

በመገኘቱ ውስጥ..!

በመገኘቱ ውስጥ..!

ዕለቱ ዓርብ ምሽት በቤ/ክያናችን የአዳር ጸሎት እየተካሄደ ነበር መንፈስ ቅዱስ በለሆሳስ ሽው! ሽው እንደሚል ነፋስ በጉባኤው ላይ ሲነፍስ ይሰማል። እዚህም እዚያም ጩኽት አለ ግንባራቸውን መሬት አስነክተው ድፍት ብለው የሚጸልዩ፣ ደግሞ ወዲህና ወዲያ ጎርደድ ጎርደድ እያሉ የሚጸልዩ ወጣት ጎልማሶች ፣ ሹል ክ ብለው መጥተው በትግርኛ ጮክ ብለው የሚጸልዩ ጥቂት ኤርትራውያንም በመካከላችን አሉ፤(ትውልድ የሚወለድበት ቤትም አይደል! Delivery room ውስጥ ጩኽት አመሉ ነው ይላሉ፤ ጩኽት ካልፈለክ semitary ሂድ ብሏል አሉ አንድ የእግዚአብሔር ሰው፤( መቃብር ቦታ ማለቱ ነው።)  ሙሉ ቤተሰቡን ይዘው ጥግትግት ብለው የሚጸልዩም አሉ ትናንሽ ልጆቻቸውም ሳይቀሩ ማለቴ ነው። መቼም እነዚህ ወላጆች  ልጆቻቸው ላይ እያደረጉት ያሉት አስተዋጽኦ ኣሌ የማይባል ነው። "ልጅን በሚሄድበት መንገድ ምራው በሸመገለ ጊዜ ከእርሱም ፈቀቅ አይልም" ይል የለ መጽሐፍ! በእነዚሁ የምሽት ጸሎቶች ላይ በመሃል መስመር 2ኛ መደዳ ላይ በጉልበቷ ተንበርክካ፡ አልያም በሆዷ ተኝታ የመጸለይ ልማድ ያላት ከሁለት ትንንሽ ልጆቿ ጋር መጥታ የምትጸልይ እህት አለች።ልጇ ህመም የጀመራት ገና የ3 ወር ህጻን ሳለች ነበር እስከ 4 ዓመቷ ድረስም በመታመሟ በርካታ ዶላሮችን ለመድኃኒት፣ለህክምና ጨርሳለች ። በጣም ውድ የሚባሉ መድኅኒቶችን በየጊዜው ትወስዳለች።  የህመሙ ዓይነት ኤር ዌይ ዲዝዝስ (air way diseases) ይባላል። አተነፋፈስ ላይ ያለ ከፍተኛ ችግር ነው ፤ ህመሙ ሽቶ፣ የቡና፣የምግብ..ወዘተ ሽታዎችን የማይወድ በመሆኑ ቤት ውስጥ እነዚህ ነገሮች መጠቀም ለረጅም ጊዜ አዳግቷል። ሰው ቤት  ወይም ቤ/ክ መሄድ ከዚህ ጋር ተያይዞ ባለ ችግር ምክንያት ነጻነታቸው ተነፍጎ የኖሩ ቤተሰቦች ናቸው። እስከመቼ? የሚልጥያቄ አላት።.. ጸሎትን የሚሰማ አምላክ አንድ ምሽት ልመናዋን ሰምቶ ፈረደላት፤ መንፈስ ቅዱስ ልጇን በፈውስ ሲጎበኝ በቅርብ ሆኜ አይቻለሁ ። በዚያን ምሽት ቮሚት  አደረገች ለዓመታት ያስቃያት ህመም ንቅል ብሎ ጠፋ! ይህ ከሆነ ይኽው ዛሬ ድፍን አንድ ዓመት ሞላው። ሽቶ፣ የምግብ፣ የቡና ሽታ የሚባል ችግር ታሪክ ሆኗል። ...ጌታ ስለሰራላት ነገር በጉባኤ ፊት ቀርባ ስትመሰክር እንዲህ አለች፡ "መንፈስ ቅዱስ በመካከላችሁ በኅይል እየሰራ ነው፤ እናንተ ግን  አልተዘጋጃችሁም!"  ይህን ያለችው ፈውስ ይኖራል ብለን ... አንዳንድ ዕቃዎችን ገዝተን ባለማስቀመጣችን ነበር። ..  አዎ! በየሐሙሱና ዓርብ የሚፈወሰው ሰው ቁጥር እየጨመረ ነው፤  ጌታ በመካከላችን እየሰራ ነው። የሚበልጠውም ነገር ገና ከፊት አለ! በዚህች እህት ቤት ሌላም የሆነ ተዐምር አለ፤ ነገሩ እንዲህ ነው፡ ከዕለታት አንድ ቀን ባለቤቷ የአባቱን ሞት መርዶ ሰምቶ እቤት ተቀምጧል!ተብለን የቤ/ክ አገልጋዮች ተጠራርተን ቤቷ ሄድን፤ በእርግጥ በሰዐቱ ባለቤቷ ቤት ውስጥ አልነበረም፤  ነገር ግን ለቅሶ ሊደርሱ የመጡ ሌሎች ሰዎች ስለነበሩ ከእነርሱ ጋር  ተዋወቅን፤በተለይ አንደኛዋ ክርር ያለ ሙስሊም ባግራውንድ የነበራት ሴት ነች። ሳዑዲ ድረስ በመሄድ እስልምናን የሚያጸኑ አንዳንድ ስርዓቶችን የፈጸመች....ይሁንና ስለክርስቶስ ተመሰከረላት ልቧ ተነካ፤ በስጋ ያላት ሃብቷ ወይም የቤተሰብጉዳይ አልያዟትም፤ብዙ ነገሮችን  ቤቷ ጠርታ አስረከበችን። ህይወቷ ተለወጠ! በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም ጌታ ያዘዘውን ጥምቀት ተጠምቀች፤.. አሁንማ ሌሎች ወደ ጌታ እንዲመጡ ተግታ እየሰራች ነው...ስለ ጌታ ፍቅር ስትናገር "ብዙ ነገሬ የተቀረፈበትን የቤ/ክ ን የጾም ጸሎት ቀን መቅረት እንዴት ይሆንልኛል? ትላለች። ሁላችን የእግዚአብሔርን ፊት ሁልጊዜ ብንሻ አንድ ቀን ከመልሳችን ጋር ወደ ቤታችን እንመለሳለን። ዳዊት " ቆይቼ እግዚአብሔርን ደጅ ጠናሁት እርሱም ዘምበል አለልኝ፡፡" እንዳለ እኛም ፊቱን በመፈለግ እንትጋ!  በመካከላችን በኃይል እየሰራች ያለችውን የእግዚአብሔርን ጣት እንናፍቅ!  እንምጣና በመገኘቱ ውስጥ እንሁን!! ሪቫይቫል ይቀጥላል....

<<Let us be witnesses for Christ!>>
     

No comments:

Post a Comment